Latest

የቢቢሲ የምርመራ ቡድን ቻይና ሙስሊም ዜጎቿን በማጎሪያ እያሰቃየች እንደሆነ ደርሶበታል - ቢቢሲ



ቻይና ለሙስሊም ዜጎቿ ምድራዊ ሲኦል ሆናለች
ቻይና ለሙስሊም ዜጎቿ ምድራዊ ሲኦል ሆናለች
ወትሮም ቻይና ለምዕራባዊያን ምስጢር ናት። ለሙስሊም ዜጎቿ ደግሞ ጀሐነም። የቢቢሲ የምርመራ ዘገባ ቡድን ይፋ ባደረገው ልዩ ጥንቅር ቻይና በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሙስሊም ዜጎችን የምታጉርበት የበረሃ ካምፕ መኖሩን አጋልጧል።
"የዕደ ጥበብ ማሰልጠኛ" በሚል ሽፋን ለዓመታት የቆየው ይህ ካምፕ አስተሳሰብን የሚያጥብ፣ ጉልበትን የሚያዝል፥ እምነትን የሚሸረሽር፣ ኅቡዕ የግዞት ማዕከል ነበር ተብሏል።

እንደ ቢቢሲ ዘገባ ከሆነ በማዕከሉ ገብተው የሚወጡ ዜጎች ሃይማኖታቸውን ብቻ ሳይሆን ጨርቃቸውን ሊጥሉ ይችላሉ።

ቻይና በበኩሏ "የአክራሪ ሙስሊሞች ሞገደኛ አስተሳሰብ የምገራበት ከፍተኛ የትምህርትና ሥልጠና ተቋሜ ነው" ትላለች።



ካምፑ የት ይገኛል?

ዢንዣንግ በሚሰኘው የምዕራብ ቻይና ክፍለ ግዛት ዳባቼንግ በምትባል ትንሽዬ አውራጃ ይገኛል፤ እልም ባለ በረሃ ውስጥ።

የዚህ የግዞት ማዕከል አጥር ሁለት ኪሎ ሜትር ይረዝማል፣ 16 ሰማይ ጠቀስ የጥበቃ ማማዎችም አሉት።

ቻይና የገዛ ሙስሊም ዜጎቿን እያፈነች በዚህ የግዞት ካምፕ ስታሰቃይ እንደኖረች የማያወላዳ መረጃ ተገኝቷል።

የማጎሪያ ካምፑ የሳተላይት ምሥል
የማጎሪያ ካምፑ የሳተላይት ምሥል

እንዴት ተደረሰበት?
ከ2015 ወዲህ በዚህ ጭው ያለ በረሃ የግንባታ ቁሳቁሶች ሲንቀሳቀሱ ግርምትን ፈጥሮ ነበር፤ በዚህ ስፍራ ምን ይገነባ ይሆን? የሚሉ ጥርጣሬዎች የበረከቱበት ጊዜም ነበር።

ከሚያዚያ 2018 ወዲህ ግን የሳተላይት ምሥሎች አንዳች ግንባታን ማሳየት ጀመሩ።

እጅግ ግዙፍ፣ ከፍተኛ ጥበቃ የሚደረግለት የበረሃ ካምፕ መሆኑም ተረጋገጠ።

አጥሩ ብቻ 2 ኪሎ ሜትር ይረዝማል። እስከ አፍንጫቸው የታጠቁ በሺ የሚቆጠሩ የሰው 'ዋርዲያዎች' የሚኖሩበት፣ 16 የስለላ ማማዎች የተቸነከሩበት ካምፕ።

ያም ሆኖ በዚህ ዘመን ከተፈጸሙ የጅምላ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች አንዱ በዚህ በረሃ እንደሚፈጸም የሚያውቅ አልነበረም።

የቢቢሲ የምርመራ ጉዞ ዘገባ
የቢቢሲ የምርምር ጋዜጠኞች ቡድን በማለዳ ኡሩምኪ አየር ማረፊያ ደረስን።

ቡድናችን ከአየር መንገድ ወጥቶ ወደ ደባቼንግ እስኪደርስ ድረስ ቢያንስ አምስት መኪናዎች እየተከታተሉን ነበር። ከነዚህ ውስጥ ብዙዎቹ ነጭ ለባሾች ነበሩ።

ወደዚህ ካምፕ የመጠጋቱ ነገር ለመርማሪ ቡድኑ ፈተና እንደሚሆን ሳይታለም የተፈታ ነው። ወደ ሥፍራው እየተቃረብን ስንመጣ አንዳች ኃይል እንደሚያስቆመን ገምተን ነበር። በመቶ ሜትሮች ርቀት ካምፑን ስንቃረብ ያልጠበቅነውን ተመለከትን።

ያ በሳተላይት የአሸዋ ቁልል ይመስል የነበረው መጋዘን ሌላ መልክ ይዟል። ከጎኑም የማስፋፊያ ፕሮጀክት ግንባታ እየተካሄደ ነበር።

ክሬኖች፣ ስካቫተርና ሌሎች የግንባታ መሣሪያዎች ይንኳኳሉ። በመልክ የተሰደሩ ባለ አራት ፎቅ ቡላማ ሕንጻዎች ይታያሉ።

ይህ ሁሉ ጭው ባለ በበረሃ ውስጥ የሚታይ ትዕይንት ነው።

ካሜራችን መቅረጽ እንደጀመረ ከየት መጡ ሳንል ፖሊሶች ወረሩን። መኪናችን በደኅንነቶች እንዲቆም ተደረገ። ካሜራችንን እንድናጠፋ ቀጭን ትዕዛዝ ተሰጠን።

ያም ሆኖ ካሜራችን አንድ ምስል አስቀርቶ ነበር። ዓለም ምንነቱን የማያውቀውን ካምፕ ምስል።
እነማን ይታጎሩበታል?
በቻይና ምዕራባዊ ክፍል የሚገኝ ሶላት የማይሰገድበት መስጊድ
በቻይና ምዕራባዊ ክፍል የሚገኝ ሶላት የማይሰገድበት መስጊድ

ወደዚህ ካምፕ ለመወርወር ቻይናዊ ሙስሊም መሆን በቂ ነው።

የአካባቢው ተወላጆችን ስለዚህ ካምፕ ምንነት ስንጠይቃቸው በፍርሃት ይደነብሩ ነበር። ገሚሶቹ ደግሞ ትምህርት ቤት እንደሆነ ብቻ ይናገራሉ። ከዓለም ዕይታ የተደበቀ ትምህርት ቤት።

"በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች፤ በአስተሳሰብ ጤና የራቃቸው ሰዎች የሚማሩበት ነው" አለን ሌላ ነዋሪ።

ቻይና በተደጋጋሚ ሙስሊም ዜጎቿን ማጎርያ ውስጥ እንደማትወረውራቸው ስታስተባብል ኖራለች።

ይህን ክስ ተከትሎ የቻይና ቴሌቪዥን በፕሮፓጋንዳ ተጠምዷል። ንጹሕ መማሪያ ክፍሎችን፤ አመስጋኝ ተማሪዎችን ወዘተ በማሳየት።

ሆኖም በዚህ ትምህርት ቤት መመረቅ የለም፤ ግዞት ነው። መግባት እንጂ መውጣት ሕልም ነው።

በቴሌቪዥን የሚቀርቡት ተማሪዎችም ይህ "ትምህርት ቤት" እንዴት ሕይወታቸውንና መንፈሳቸውን እንዳደሰ ነው የሚናገሩት። ነገርየው ቃለ መጠይቅ ሳይሆን ኑዛዜ ነበር።

ይህ ማጎርያ የተገነባው በተለይ ለዢያንዣንግ ነዋሪዎች ነው፤ ኢጉርስ ይባላሉ። ብዙዎች ከአናሳ የቻይና ዘውግ የተገኙ ናቸው። 1.5 ቢሊዮን ከሚሆነው የቻይና ሕዝብ 10 ሚሊዮን ቢሆኑ ነው።

ቻይንኛን አይናገሩም። ቋንቋቸውም ቱርኪክ ነው።

የዚህ ግዛት ሙስሊም ነዋሪዎች ነጠላ ማጣፋት ሻሽ ማገልደም፥ በሂጃብ መጀቦን አይሞክሯትም።

ረመዳን መጾም በጠኔ ያስገርፋል፣ ሶላት መስገድ ለግዞት ይዳርጋል። ጢንም ማንዠርገግ ከፍተኛ የሥነ ምግባር ጥሰት ነው።

ቻይና ክፍል ሃይሞኖት አንድ ነው፤ እሱም ኮሚኒዝም፤ መማለድም በሺ ዣን ፒንግ።

አብዱልሰላም ሙሐሜት
አብዱልሰላም ሙሐሜት

ምስክርነት
ቢቢሲ ስምንት ከሚሆኑ የኢጉር ዘውግ አባላት ጋር ቃለ ምልልስ አድርጓል። ነዋሪነታቸው ከቻይና ወዲያ ባሕር ማዶ ነው።

ምስክርነታቸው መርማሪ ቡድኑ ከደረሰበት ውጤት ጋር ስምም ነው።

አብዱሰላም ሙሐመት የ41 ዓመት ጎልማሳ ነው። ቀብር ላይ የቁርዓን ጥቅስ ተናግረሃል በሚል በ2014 ወደ ካምፑ መወሰዱን ያስታውሳል።

"በካምፑ ውስጥ በጠዋት ተነስተህ ትሰለፋለህ። ከባድ የሰውነት እንቅስቃሴ እንድትሠራ ትገደዳለህ። በፍጥነት ትሮጣለህ። በፍጥነት መሮጥ ያልቻሉትን ማሰቃያ ራሱን የቻለ ክፍል አለ" ይላል ሌላው የቀድሞ ታራሚ አብሌት ሱርሱን።

"ሁልጊዜ መዝሙር ያዘምሩናል፤ 'ደሜና አጥንቴ ለኮሚኒስት ፓርቲ፤ ቻይና ትቅደም' የሚል መዝሙር። ሕጎችን ያሸመድዱናል። ያስተማሩንን በደንብ ካላስታወስን ግን ከፍተኛ ቅጣት ይጠብቀናል።" ይላል አብሌት።

አብሌት በለስ ቀንቷቸው ከግዞት ካምፑ ማምለጥ ከቻሉ እድለኛ ዜጎች አንዱ ነው። አሁን በቱርክ አገር ጥገኝነት ጠይቆ ይገኛል።

"እኔ እዚያ ሳለሁ የ74 ዓመት አዛውንት ከ8 ልጆቻቸው ጋር ፍዳቸውን ያዩ ነበር፤ ሙስሊም የሆነ አንድም ቻይናዊ የቀረ አይመስለኝም" ሲል ምስክርነቱን ሰጥቷል።

ሶላት የማያውቁ መስጊዶች

መስጊዶች ለቱሪስቶች የጉብኝት መዳረሻ እንጂ ሶላት መስገጃ አልሆኑም
መስጊዶች ለቱሪስቶች የጉብኝት መዳረሻ እንጂ ሶላት መስገጃ አልሆኑም

የቢቢሲ የምርመራ ጋዜጠኞች ቡድን ቀድሞ የኡግር ባሕል ማዕከል ተደርጋ በምትታሰበው ካሻጉር በተባለችው ከተማ ቅኝት አድርጎ ነበር።

በዚች ከተማ የሚገኙ ሰዎች ቤተሰቦቻቸው ወዴት እንደሄዱ ሲጠየቁ ለመናገር ይፈራሉ። የከተማው ነዋሪ ግዞት ነው ያለው።

የከተማዋ ትልቁ መስጊድ ወደ ሙዝየምነት ተቀይሯል።

መርማሪ ቡድኑ የዙሁር ሶላትን ለማየት መስጂድ በር ላይ ነበር። ለሶላት ብቅ ያለ የለም። አዛንም የለም።

መስጊዱ በር ላይ ቆሞ የነበረ አንድ ፖሊስ " ሶላት ስንት ሰዓት ነው የሚጀመረው" ብለን ጠየቅነው። " ስለ ሶላት የማውቀው ነገር የለም፤ እዚህ ያለሁት ቱሪስቶችን ለመርዳት ነው" አለ።

ከመስጊዱ አቅራቢያ ጢማቸውን ሙልጭ አድርገው የተላጩ ሸምገል ያሉ ሰዎችን ተመለከትን። "ሰጋጆች ወዴት ጠፉ?" ስንል ጠየቅናቸው።

አንደኛው አዛውንት ዝም እንድንል በእጃቸው ምልክት ሰጡን። ሌላኛው አንሾኳሸኩ "ኸረ መስጊድ የሚመጣ ሰው የለም!"

ወደ መስጊዱ በር በመመለስ ደጃፉን የሚያጸዳ ፖሊስ ዘንድ ሄድን።

ቱሪስቶች ከመስጊዱ እየተጠጉ ፎቶ ይነሱ ነበር። መስጊዱ ለቱሪስት እንጂ ለሶላት ሰጋጆች ቦታ የለውም። ሶላት ሰጋጆች ግዞት ተወስደዋል።

No comments