Latest

«ኦሮሞ እና አማራን የሚነጣጥሉ አይሳካላቸውም» የኦሮሞ ድርጅቶች

የኦሮሞ ድርጅቶች

የኦሮሞ ሕዝብ አንድነት እና አንገብጋቢ የወቅቱ ጉዳዮችን አስመልክቶ ኦነግ፣ ኦፌኮ፣ የተባበሩት ኦነግ፣ የኦሮሚያ ነፃነት አንድነት ግንባር እና የኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ግንባር የጋራ መግለጫ አውጥተዋል።

ፓርቲዎቹ በጋራ ባወጡት መግለጫ አምስት ዋና ዋና ነጥቦች ላይ አተኩረዋል።

አነሱም የኦሮሞ ማንነትን ለማጥፋት እየተደረገ ያለው ሙከራ፣ አዲስ አበባ ጉዳይ፣ ሕዝብን ከሕዝብ የሚያጋጩ ሚድያዎች፣ በሃገሪቱ እየታየ ያለው ለውጥን እና በቋንቋ ላይ የተመሰረተ ፌዴራሊዝምን የሚመለከቱ ናቸው።

  • የ ኦሮሞ ማንነት
ፓርቲዎቹ ሰሞኑን አደርግነው ባሉት ውይይት «ጠላቶቻችን የኦሮሞን ሕዝብ ለማጥፋት አሰቃቂ ግድያ ከመፈፀም አልፎ በኦሮሞ ሕዝብ ሰም የሚጠሩ ተቋማትን በማውደም ከፍተኛ ዝርፍያ ፈፅመዋል» ብለዋል።

«ከዚህ ጀርባ ፀረ ኦሮሞ አቋም ያለው የተደረጃ የፖለቲካ ቡድን ስለመኖሩ የሚያመለክቱ በርካታ መረጃዎች ተገኝተዋል» ይላል መግለጫው።

«በማንነታችን ላይ የተቃጣውን ድርጊት ከማንኛውም ጊዜ በላይ እናወግዛለን፤ ድርጊቱን የፈፀሙ በህግ እንዲጠየቁ እንጠይቃለን» በማለት ፓርቲዎቹ መግለጫቸው ላይ አትተዋል።
  • አዲስ አበባ ን በተመለከተ
«ዛሬ አዲስ አበባ የምትገኝበት ሥፍራ የጥንት የኦሮሞ ጎሳዎች የእምነት፣ ፖለቲካ እና ኢኮኖሚ ማዕከል የነበረ መሆኑ አይካድም» የሚለው መግለጫው «ጎሳዎቹ መሬታቸውን ተነጥቀው እንዲጠፉ ተደርገዋል» ሲል ያክላል።

ፓርቲዎቹ «እኛ ኦሮሞ ድርጅቶች አዲስ አበባ ሁሌም የኦሮሞ ሕዝብ ናት፤ ይህ ማለት ግን ከኦሮሞ ውጭ መኖር አይችልም ማለት አይደለም» ሲሉ በመግለጫቸው አትተዋል።

«ሆኖም አንዳንድ የፖለቲካ ድርጀቶች ይህን በመካድ ከተማዋን እያሸበሩ መሆናቸውን ታዝበናል፤ አልፎም በኦሮሞ እና አማራ ሕዝብ መካል ጥርጣሬ እንዲፈጠር ደፋ ቀና እያሉ ይገኛሉ። ቢሆንም አይሳካላቸውም፤ የኦሮሞ እና የአማራ ሕዝቦች ለውጥ ለማምጣት አብረው ታግለዋልና» ይላል መግለጫው።

መላው ሕዝብ የእኒህን ኃይሎች ሴራ ለማክሸፍ አብሮ መቆም አለበትም ሲል መግለጫው ያክላል።


  • ሕዝብን ከሕዝብ የሚያጋጩ ሚድያዎች
ለወገናዊ ፖለቲካ የሚያደሉ ሚድያዎች ሕዝብን ከሕዝብ ለማጋጨት ተግተው እየሰሩ እንደሆነ መግለጫው አትቷል።

«ስለዚህ ውጭም ሆነ ሃገር ቤት ያላችሁ ሃገር አማሽ ሚድያዎች በህግም በታሪክም ፊት ተጠያቂ መሆናችሁን አውቃችሁ ከድርጊታችሁ ታቀቡ» በማለት መግለጫው አስገንዝቧል።
  • በሃገሪቷ እየታየ ያለውን ለውጥና ሽግግር በተመለከተ
«በሃገሪቱ ውስጥ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየታየ የመጣውን ለውጥና ፖለቲካዊ መነቃቃት ለውጡን በሚፈልጉ የሥርዓቱ አካላት የተገኘ እንደሆነ እናምናለን» የሚለው መግለጫው በዚህ የሽግግር ወቅት ስልጣን ላይ ያሉ አካላት ዘላቂ ለውጥ እንዲያመጡ ሁኔታዎችን እናመቻቻለን» የሚል አቋም ይዟል።

«ነገር ግን እንደማይሳካላቸው የተገነዘቡ የፖለቲካ ቡድኖች በሃሰት የብር ኖቶች ዜጎችን በማታለል የሃይማኖትና የብሄር ግጭት በማስነሳት መንግስት የሌለ ለማስመሰል እየተሯሯጡ እንደሆነ ግልጽ ነው።»

«በመሆኑም አሁን ያሉ ተቋማት በህገ መንግሥቱ መሰረት በትክክል እንዲሰሩ ተደርጎ በነጻ፣ ተአማኒና በቂ ፉክክር በተደረገበት ህዝባዊ ምርጫ ወደ ዴሞክራሲ የሚደረገውን ሽግግር ብቻ የምንደግፍ መሆኑን እንገልጻለን» ሲሉ ድርጀቶቹ አቋማቸውን አንፀባርቀዋል።
  • በቋንቋ ላይ የተመሰረተ ፌደራሊዝምን በተመለከተ
ለዘመናት ኢትዮጵያ ውስጥ የነበረውን የህዝቦች የማንነት ጥያቄ ለማክበር የተዘረጋውን የፌደራሊዝም ሥርዓት ደንታ የሌላቸው ኃይሎች ሥርዓቱ የችግሩ መንስኤ እንደሆነ አድርገው ለማቅረብ እየሞከሩ ነው ሲል መግለጫው ይወቅሳል።

አንዳንድ ሚዲያዎችም ይህንኑ ተግባር ተያይዘውታል። ስለዚህ እኛ የኦሮሞ የፖለቲካ ድርጅቶች ፈጽሞ የማንቀበለው መሆኑንና በህልውናችን ላይ የተቃጣ አደጋ አድርገን እንደምንመለከተው እንገልጻለን በማለት ድርጀቶቹ መግለጫቸውን አጠናቀዋል።

No comments