Latest

ሸገር ደርሶ መልስ (ክንፉ አሰፋ)

ሸገር ደርሶ መልስ (ክንፉ አሰፋ)

(የጉዞ ማስታወሻ በተለይ ለኢትዮጲስ)
ገና ጎህ አልቀደደም። ቅላጼውን የዘነጋሁት የተቀላቀለ ድምጽ በጆሮዬ ውል እያለብኝ በእንቅልፍ እና በሰመመን መሃከል ነኝ። የጥዋትዋ ጸሃይ ጨለማውን ልትገፍ እየዳኸች ባለበት ቅጽበት ከግራና ቀኝ የሚሰማው ነገር ከነበርኩበት ሰመመን ሲያነቃኝ ይታወሰኛል።  


ወትሮውን ከእንቅልፍ ስነቃ የምሰማው የተሽከርካሪ ድምጽ ስላልነበር ለአፍታ ግራ ተጋባሁ። በዚህች ጣፋጭ ማለዳ አኩኩሉ የሚል የዶሮ ድምጽ ሰማለሁ፣ መንፈስን የሚያድስ የአእዋፍ ዝማሬም አደምጣለሁ፣ ከወንዝ እና ኩሬዎች የሚመጣ የእንቁራሪት ጩኸት… ወዘተ ተደምሮ 20 አመታት ወደ ኋላ መለሰኝ።

ከእንቅልፌ እንደነቃሁ የተቀላቀለ ስሜት ነበር የተሰማኝ። ላለፉት ሶስት አስርተ-አመታት ተፈጥሮ የለገሰችኝ መብቴን ብቻ ሳይሆን ሃገሬንም ተቀምቼ እንደነበር አስተዋልኩ።  

ጥቂቶች በሃገሪቱ አናት ላይ ሆነው ፍርድ ሲሰጡ፣ ያሻቸውን ሲያደርጉ፣ ሲፈልጡ እና ሲቆርጡ፣ ኢትዮጵያዊነቴን የቀሙበት ዘመን ማብቃቱ ሳስተውል ደግሞ ደስታዬ ጣራ ነክቷል። የአማርኛ ቋንቋ በሚነገርበት ጢያራ ውስጥ ተሳፍሬ ወደ ሃገሬ ከገባሁባት ደቂቃ ጀምሮ፣ ለሃገሬ እና በሃገሬ ላይ ባእድ የመሆን ስሜቴ እየተገፈፈ ነው።

“በህይወት እያለሁ ለሃገርህ ትበቃለህ ብዬ አላሰብኩም ነበር። ከአሁን በኋላ ብሞት፣ ምንም አይመስለኝ!” የሚለው የእናቴ ንግግር ከውስጥ የመጣ ስለነበር መንፈሴን ረበሸው። ሃገሬን እና ዜግነቴን ያስነጠቀኝ ወንጀል ተፈጥሮ የለገሰችኝ የመናገር መብት መሆኑን ሳስብ ደግሞ የበለጠ ተረበሽኩ። መናገር እና መጻፍ ጥቂቶች ከኪሳቸው እየቆነጠሩ የሚሰጡን መብት ነበር።

በተቀላቀለ ስሜት የታጨቀው የመጀመርያው ቀን አለፈ። በሰው ሰራሽ ቁሳቁስና ቅሪተ-ምርት ያልተበከለ አየር እየተነፈስኩ መሆኑ በግልጽ ይታወቀኛል። በመስኮት በኩል አጮልቃ የምትገባ የጥዋት ጸሃይ ፍንጣቂ ስመለከት፣ የሃገር ቤትዋ የማለዳ ድባብ ምን ያህል ናፍቃኝ እንደነበር አስተዋልኩ። 

የማያውቁት አይናፍቅም እንዲሉ የረሳሁት የመሰለኝ ሃገርኛ ስሜት ዳግም አንሰራራ። ይህን ስሜት በቃላት ለመግለጽ ይከብደኛል።

ከ20 አመታት በኋላ ያገኘኋት እናቴ ማልዳ ተነስታ ወደ ቤተክርስቲያን ሄዳለች። ስለትዋን ልታደርስ። ለአምስት ታቦት፣ ጃንጥላ እና ጧፍ እንደተሳለች ነግራኝ ነበር። ባልታሰበ ሰዓት እና በልተጠበቀ ግዜ በአይነ ስጋዋ ስታየኝ በፍጹም አላመነችም።  

ከአይኖችዋ የሚዘንበው የደስታ እንባ፤ ደንዞ የነበረውን የኔን ስሜትም በእጅጉ መንካቱን መሸሸግ አልቻልኩም። ከአባት እና እናቴ፤ ከእህት እና ወንድሞቼ ጋር እንዲህ በአካል የመገናኘቱን ነገር እኔም ብሆን ረስቼው ነበር። በ“መንግስት ጠላት” ነት ተፈረጄ በጥቁር መዝገብ ላይ የነበረው ስሜ እስኪሰረዝ ድረስ ወደ ሃገሬ መግባቱን ነገር ከአእምሮዬ አውጥቼዋለው። እርግጥ ነው። 

እትብቴ ከተቀበረባት ምድር እጅግ ርቄ በባእድ ሃገር ስኖር የጎደለብኝ ነገር አልነበረም። እኔን የራበኝ የሃገር ፍቅር ነው። ወገን ሲሰቃይ እና ሲያዝን የስሜቱ ተካፋይ መሆን ያለመቻል ነው የሚያመኝ። በአካል ነጻ ብሆንም በህሊናዬ ግን እስረኛ ነበርኩ።

የእልልታ ድምጽ ሰምቶ ግቢያችንን የሞላው የሰፈር ሰው ሁሉ ፈጣሪን ሲያመሰግን ሰማሁ። ከፈጣሪ ቀጥሎ ደግሞ የሚመሰገነው ዶ/ር ዐብይ አሕመድ ነበር። “እድሜው ይርዘም” ሲሉ ይመርቁታል የሚያገኙኝ ሁሉ። የስጦታ እጄን በዘረጋሁ ቁጥር እንኳ የምመሰገነው እኔ አልነበርኩም። “እሱ እንደ መላክ ከሰማይ ባይመጣልን ኖሮ ይህንን ማን ያደርግልን ነበር?” ይሉኛል።

እርግጥ ነው። ሁሉም እንደነበረ አይቆይም። የግዜ ጉዳይ እንጂ ለውጥ የሚቀር ነገር አይደለም። ተፈጥሯዊ ነውና። ሕዝቡ ላይ የሚታየው ለውጥ ግን እጅግ ያሳዝናል። ለሁለት አስርተ አመታት የተለየሁት ወገኔ እድገቱ ሽቅብ ሳይሆን ቁልቁል ሆኖ ነው ያገኘሁት። የሃዘንም ሆነ የደስታ ወቅት ነበረው።  

 በልቅሶ ግዜ ሃዘኑን፣ በደስታ ግዜ ደግሞ ደስታውን መካፈል ባለመቻሌ አዝናለሁ። የዘመድ አዝማድን ሃዘን በባእድ ሃገር ሆኖ መስማት፣ ይህንን ያለመካፈል ምን ያህል እንደሚከብድ በውል የሚያውቀው ሃዘኑ የደረሰበት ብቻ ነው። አብዛኞቹ የሰፈር ሰዎች በህይወት የሉም። ጥቂት የቀሩት እጅግ ተጎሳቁለዋል። 

ከሰውነት ተራ ታወጣቸው ችግር ሁለመናቸውን በልቶባቸዋል። ውበታቸውን፣ ፈገግታቸውን፣ ልጆቻቸውን ሳይቀር ወስዶባቸዋል። ድህነት ብቻ የማይገልጸውን ይህንን ጉዳይ በዚህ ማስታወሻ ብቻ አንስቼ አልጨርሰውም። ይህ ራሱን የቻለ ትልቅ ቅጽ ይወጣዋል።

የናፈቀችኝ ሀገሬ እንደገባሁ አልቦዘንኩም። ከከተማ እስከ ገጠር እየተጓዝኩ እየተነገረን የነበረውን እድገት እና ትራንስፎርሜሽን አስተዋልኩ። ከሸራተን እስከ ቡሌ ትርፍራፊ ምግብ መሸጫ፤ ከዘመናዊ ቪላ እስከ ላስቲክ መኖርያ ያለውን የኖሮ ልዩነት እየታዘቡ ብዙ ነገር መናገር ይቻላል። በሃያ አመት ብዙ ነገር ተለዋውጧል። ልብ በሉ! እዚህ ላይ የማነሳው ለውጥ እንጂ እድገት አይደለም። ሁለቱ ፍጹም የተላያዩ ነገሮች ናቸው። ከአብዛኛው ሕዝብ ፊት ላይ ጉስቁልና ይነበባል። ዝቅ ብሎ ለሚመለከት ደግሞ ለሰው ልጅ መሰረታዊ የሆነው ምግብ እና ልብስ እንኳን እጅግ ብርቅ መሆኑን ይረዳል። ስኳር እና ዘይት ደግሞ ቅንጦት መሆን ጀምረዋል።

ከሸራተን ብዙም ሳይርቅ የሚገኘው የቡሌ መሸጫ ስፍራ የድህነቱን ጥልቀት ይነግረናል። ቀደም ሲል በመገንኛ ብዙሃን የሰማሁትም የፍርፋሪ እና ትርፍራፊ ምግብ ገበያ ጉዳይ በማየት ማመኑ ግድ ይላል። ከምግብ ቤቶች የሚጣል ትራፊ እየተመገበ የሚኖር ወገን ቁጥር ቀላል አይደለም። ሌላም ትዝብት አለ። ጉርሻ የሚሸጥበት ታሪካዊ ዘመን ላይ ያደረሰን የእድገት እና ትራንስፎርሜሽን!

የውሃ እና መብራት መቋረጥ እንግዳ የሚሆነው ከውጭ ለሚመገባው ሰው ብቻ ነው። የሃገሬው ሕዝብ ችግሩን ከመልመድ አልፎ ተቀብሎታል። ውሃ ለሳምንት ያህል ካልተቋረጠ እጅግ ይደንቃል፤ መብራትም በቀን ቢያንስ አንዴ ካልጠፋ ነው ለሰው የሚገርመው።

መንገዶች ተቀያይረዋል። የተቦደሱ መንገዶች ጥገና ስለማይደረግላቸው ተሽከርካሪዎቹ አፍ አውጥተው መናገር የቀራቸው ይመስላል። በአዲስ አበባ ከተማ ያላለቁ ህንጻዎች እዚህም እዚያም እንደ ጅብራ ተገትረዋል። የአብዛኞቹ ሕንጻዎች (በተለይ ቦሌ) ባለቤት የህወሃት ካድሬዎች እንደሆኑ ከአስጎብኛችን ታረዳን። 

የህወሃት ሰዎች፣ በአንዲት ጀንበር ሚሊዮን በሚኮንበት በወርቃማው ዘመን ያስገነቡት ሕንጻ! አልቀው ስራ ያልጀመሩ ሕንጻዎችም ቁጥር ቀላል አይደለም። ከውጭ ሲታይ ዘመናዊ የሚባል ፎቅ ውስጡ ግን ኦና ነው። ባለ ሰባት ፎቅ ኮንዶሚንየም ሊፍት የለውም። የመብራት እና ውሃ መስመር እንኳ አልተዘረጋለትም…..

ከአዲስ አበባ 335 ኪሎ ሜትር ርቃ የምትገኘው ጂማ አባጂፋር እንደከተማ ወድቃለች። የውጭ ምንዛሪ ቡናችንን የምታመርት ሃገር ባታድግ እንኳ ቢያንስ እንዳለች ጠብቂያት ነበር። የማገኛቸው ሁሉ “ሙክታር ከድር እና አስቴር ማሞ ግጠዋታል!” ይሉኛል። 

 በ20 ዓመታት ግዜ ውስጥ በዚህች ከተማ የተለወጠ ነገር ቢኖር ቁቤ እና ባጃጅ ብቻ ነው። ላቲን አማርኛን ተክቶታል። ይህ እንዲሆን መደረጉ የሚቃወም የለም። ግና ይህ ለከተማዋም ይሁን ለህብረተሰቡ እድገት ያደረገው አስተዋጽዖ ምን እንደሆነ የሚነግረኝ አላገኘሁም።  

በሕዝቡ ስነ ልቦና እየተጫወቱ የልባቸውን የሚያደርሱ ጅቦች ብቻ በሂደቱ መጠቀማቸውን የሚክድ ግን የለም። ዛሬ ሁሉም ዶ/ር ዐብይ አህመድን ከመውደድ አልፈው ማምለክ የጀመሩ ይመስላል።

ጂማ አባጂፋር አውሮፕላን ማረፊያ ቅርስ ይመስል ሳይነካ ተቀምቷል። ሳይታደስ፤ ሳይደለዝ። በአደራ የተቀመጠ የሚመስለው የጥንት ህንጻ ሁሉ እንደ መዛግም ያደርገዋል። የፈረንጅ አራዳ ህንጻዎች ጣልያን እንዳስቀመጣቸው ነው ያገኘሁዋቸው።

መሰረታዊ የሆኑ ውሃ እና ኤሌክትሪክ አሁን ብርቅ እና ቅንጦት እየሆኑ መጥተዋል። በደርግ ግዜ በከተማዋ መብራት ለድቂቃ እንኳ ተቋርጦ እንደነበር አላስታውስም። ህወሃት ስልጣን ከያዘ ወዲህ ትልቁን የሃይል ማመንጫ (ጀነሬተር) ያለ ምንም ምክንያት ወደ መቀሌ ወስዶታል። 

የዳቦ ስም ወጥቶለት በህወሃት እንደ ከብት ሲነዳ የነበረው ኦህዴድ ይህ ግዙፍ ማሽን ሲዘረፍ አብሮ ይሸከም ነበር። ለስሙ “ኦሮሚያ” ከማለት ውጪ ለዚያ ሕዝብ የፈየደው አንዳች ነገር እንደሌለ ነዋሪው አሁን ላይ የተረዳው ይመስላል። ከኪሳቸው እና ከርሳቸው በላይ ማሰብ የማይችሉ እነ ሙክታር በዚህ ዝርፊያ አልተጠቀሙም ማለት አይቻልም። የአባትህ ቤት ሲዘረፍ አብረህ ዝረፍ ይላል አበው።

ከተማ ያገኘኋቸው ወጣቶች ሙክታር ከድር እና አስቴር ማሞ ከተማዋን እንደገደሏት ይናገራሉ። የኦሮሞ ሕዝብ ዲሞክራዊያዊ ድርጅት ሊቀመንበር እና የክልሉ ፕሬዝዳንት የነበረው ሙክታር ከድር በዘመድ አዝማድ ስም የገነባቸውን ሕንጻዎች እና ሆቴሎችም አሳዩኝ። 

ቦኒ ኢንተርናሽናል በሚል ሁለት ግዙፍ ሆቴሎችን እና የግሎባል ሆቴል ሕንጻዎች ለከተማዋ አዲስ ናቸው። በከተማዋ ጎላ ብለውም ይታያሉ። በእጅ አዙር የተገነቡ የሙክታር ከድር ንብረቶች።

የእድገት እና ትራንስፎርሜሽኑን ናሙና እዚያ በማጤን ጠቅላይ ሚንስትራችን የተወለዱበት ወደ አጋሮ አመራሁ። መንገዱ አይጣል ነው። ቀዳማዊ ሃይለ-ስላሴ የዘረጉት አስፋልት አፍ አውጥቶ መናገር ነው የሚቀረው። አርባ አራቱን ኪሎ ሜትር በምጥ አለፍናት። በዚያ መንገድ ላይ የሚያሽከረክሩ ሹፌሮችን ሳላደንቅ አላልፍም። 

እዚህ የተቦዳድሰ መንገድ ላይ ለማሽከርከር መንጃ ፈቃድ ብቻ ሳይሆን የሰርከስ ትምህርትም ያሻቸዋል። አጋሮ እንደ ደረስን ከተማዋ በቄሮ አመጽ ትታመስ ነበር። የኦሮሞ ወጣቶች ከንቲባው ጽህፈት ቤት ድረስ በመግባት ከስልጣን እንዲወርድ ጠየቁት።  

የውረድ – አልወርድም እሰጥ እገባው እያየለ ሲመጣ ፌደራል ፖሊስ ፈጥኖ ደርሶ ጠቃውሞውን በተነው። የቄሮ አናርኪዝም አስፈሪ እና ተግባራዊ እርምጃ መውሰዱ ያልተገባ ቢሆንም የችግሮቹን ምንጮች ማየቱ መልካም ነው።

እንደማንኛውም የህወሃት ካድሬ ማስትሬቱን በሕዝብ ሃብት ገዝቶ ወንበሩ ላይ የተቀመጠው ከንቲባ፣ ከ 41 ሺህ ለማይበልጡ የከተማዋ ነዋሪዎች ውሃ እና መብራት እንኳን ማቅረብ አልቻለም። ይህች ቡና አምራች ወረዳ የህንጻዎችዋ እና የመንገዱ መወላለቅ ተደምሮባት በጦርነት የወደመች ከተማ ነው የምትመስለው። 

ውሃ በሳምንት አንዴ ብቅ ስትል ሕዝብ ይጨፍራል። ሳይታሰብ እየጠፋ ሳይታሰብ ብቅ የሚለው የኤሌክትሪክ መብራት ችግር በአጋሮ ላይ የከፋ ሆኖ ነው የታዘብኩት። ችግሩ የገንዘብ አይደለም፣ ችግሩ የቴክኖሎጂ እጦትም አይደለም፣ ችግሩ የተማረ የሰው ሃይል ባለመኖሩም አይደለም። ችግሩ የመጣው ከአስተዳደራዊ ክህሎት ማጣት እና ከሃገራዊ ዝርፊያ ነው።

በእውቀት እና ችሎታ ሳይሆን ይልቁንም በታማኝነት እና በዘር መስፈርት ወንበሩን የያዙ የቀን ጅቦች፣ ሃገሪትዋን ከሕዝቡ ነጥቀው የግላቸው እንዳደረግኳት አስተዋልኩ….

… ይቀጥላል

No comments