Latest

በአላማጣ የማንነት ጥያቄ ባነሱ ወጣቶችና በጸጥታ ኃይሎች መካከል በተፈጠረ ግጭት የሰዎች ህይወት ጠፋ - ቢቢሲ

አላማጣ

ትናንት በአላማጣ ከተማ በታጠቀ የልዩ ኃይልና በወጣቶች መካከል በተፈጠረው ግጭት አምስት ግለሰቦች በጥይት ተመትተው መሞታቸው የዓይን እማኞች ተናገሩ።
ከጥቂት ወራት በፊት ጀምሮ የአላማጣ ከተማ ወጣቶች የማንነት ጥያቄዎችን እንደሚያነሱ የከተማው ነዋሪዎች ይናገራሉ።

አቶ ዝናቡ ማርፌ የአላማጣ ከተማ ነዋሪ ሲሆኑ ትናንት በከተማዋ በተካሄደው ሰልፍ ላይ ተሳታፊ ነበሩ። በስልፉ ወቅት ድብደባ ተፈጽሞብኛል የሚሉት አቶ ዝናቡ ''ካለፉት ሦስት ወራት ወዲህ የከተማዋ ወጣቶች ወረቀት በመበተን ሰላማዊ ሰልፎችን ለማካሄድ ጥረቶችን ያደርጉ ነበር። 


ለውጡን እንደግፋለን የሚሉ ከነቴራዎችን ያደርጋሉ በእነዚህ ተግባሮቻቸውም ይታሰራሉ ከዚያም ይፈታሉ። የትናንቱ ግን አስከፊ ነበር'' በማለት የትናንቱን ክስተት ያብራራሉ።

ትናንት የእጅ ኳስ ሜዳ ላይ በተጀመረ የተቃውሞ ሰልፍ ለበርካቶች የህይወት መጥፍት እና የአካል ጉዳት ምክንያት ሆኗል። የከተማዋ ነዋሪዎች እንደሚሉት ከሆነ መሰብሰብ አትችሉም የተባሉት የከተማዋ ወጣቶች ከፀጥታ ኃይሎች ጋር ተጋጭተዋል።

ሌላው ለደህንነቱ ሲል ስሙ እንዲጠቀስ ያልፈለገ የከተማዋ ነዋሪ በትናንቱ ግጭት በጥይት ታፋው ላይ ተመትቷል። ''በጥይት የተመታን ልጅ ለማንሳት ስሄድ እኔም ተመታሁኝ'' ይላል።

''በጥይት መመታቴን እንኳ አልታወቀኝም ነበር። አጠገቤ ያሉ ሰዎች ናቸው ስሜን እየጠሩ በጥይት መመታቴን የነገሩኝ። አንገቴ ላይ ደም ስመለከት አንገቴን የተመታሁ መስሎኝ ነበር። አንገቴ ላይ የነበረው ደም ግን የሟቹ ልጅ ነበር'' በማለት ሁኔታውን ያስረዳል።

ይህ ወጣት ትናንት ወደ የእጅ ኳስ ሜዳው ተሰባሰበው በሄዱበት ወቅት እንዲበተኑ በመደረጉ በተፈጠረ ግጭት ጉዳቱ መድረሱን ያስረዳል።

''የሆነ ነገር ያደርጉኛል ብዬ ስለሰጋሁ ወደ የግል ሕክምና እንጂ ሆስፒታል አልሄድኩም። አሁንም የምገኘው በመኖሪያ ቤቴ ነው'' ይላል።

የአላማጣ ከተማ ነዋሪው አቶ ዝናቡ እንደሚሉት የሃገር መከላከያ ሠራዊት አባላት በቦታው ቢደርሱም የዜጎችን ደህንነት ማስጠበቅ ግን ተስኗቸዋል ይላሉ።

''የልዩ ኃይሉ የሚፈጽመውን ጥቃት እንዲያስቆሙ ስንጠይቃቸው 'የተዘጋውን መንገድ ብቻ ነው የምናስከፍተው' አሉን'' ይላሉ።

የተጎጂዎች ቁጥር
ከአቶ ዝናቡ ማርፌ እና ከሌሎች የከተማዋ ነዋሪዎች እንደሰማነው ከሆነ 5 ሰዎች ተገድለዋል 15 የሚሆኑ ደግሞ ከባድ እና ቀላል ጉዳት ደርሶባቸዋል። እንዲሁም ከ50 ባለይ ሰዎች ለእስር ተዳርገዋል።

የማንነት አስመላሽ ኮሚቴ ሰብሳቢ የሆኑት አቶ አግዜ ህዳሩ በበኩላቸው የሟቾችን ቁጥር 9 የተጎጂዎችን ደግሞ 16 ያደርሱታል። የትግራይ ክልል ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ደግሞ በፌስቡክ ገጹ ላይ በአላማጣ ከተማ በማንነት ስም በሚንቀሳቀሱ አካላት እና በፀጥታ ኃይሎች መካከል በተከሰተ ግጭት የሦስት ሰዎች ህይወት አልፏል ብሏል።

ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የአላማጣ ሆስፒታል ባልደረባ ለቢቢሲ እንደተናገሩት ከሆነ በትናንቱ ግጭት ጉዳት የደረሰባቸው 25 ሰዎች በሆስፒታሉ የህክምና ክትትል እየተደረገላቸው እንደሆነ እና አንድ ሰው ደግሞ ባጋጠመው ከፍተኛ ጉዳት ለተጨማሪ ህክምና ወደ መቀሌ መላኩን ነግረውናል።
አላማጣ ዛሬ ረፋድ
አቶ ዝናቡ እና ሌላ የከተማዋ ነዋሪ እንደሚሉት ከሆነ ዛሬ እስከ ረፋድ ድረስ አላማጣ ውስጥ መንገድ ዝግ ነው። የሃገር መከላከያ ሠራዊት አባላት መንገድ ለማስከፍት ጥረት እያድጉ ነው።

ትናንት ከተገደሉት 5 ሰዎች የሁለቱ ሰኞ ጠዋት አላማጣ እየሱስ ቤተ ክርስቲያን የቀብር ሥነ-ሥርዓታቸው ተፈጽሟል። ''የሟቾች ሰውነት በከፍተኛ ሁኔታ የተበጣጠሰ ስለሆነ በጠዋት ነው የተቀበሩት'' ሲሉ አቶ ዝናቡ ነግረውናል።

ከሟቾቹ መካከል የሦስቱ ግለሰቦች አስክሬን ከአላማጣ ውጪ ወደ ሆኑ ቦታዎች የቀብር ሥነ-ሥርዓታቸው ሊፈጸም አስክሬናቸው ወደ ትውልድ ስፍራቸው መላኩን ከከተማዋ ነዋሪዎች ሰምተናል።

የማንነት አስመላሽ ኮሚቴ ሰብሳቢ የሆኑት አቶ አግዜ ህዳሩ በበኩላቸው የአካባቢው ህዝብ ላለፉት ሦስት እና አራት ወራት የማንነት ጥያቄዎችን በሰላማዊ መንገድ ለማቅረብ ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል ያሉ ሲሆን፤ ''የትግራይ ክልል መንግሥት ግን ከፍተኛ ቁጥር ያለውን ልዩ ኃይል ወደ አካባቢው በማስገባት የማንነት ጥያቄውን ለማዳፈን ወጣቶችን በማሸማቀቅ ከፍተኛ የሆነ የሥነ-ልቦና ጫና እያደረገ ነው'' ይላሉ።

አቶ አግዜ ጨምረውም ራያ አዘቦ፣ ራያ አላማጣ እና ኦፍላ የማንነት ጥያቄ የሚነሳባቸው ወረዳዎች ናቸው ብለዋል።

የትግራይ ክልላዊ መንግሥት ኮሚኬሽን ጉዳዮች ቢሮ በበኩሉ በፌስቡክ ገጹ ላይ ''የህዝብን የማንነት ጥያቄ በማስመሰል ሌላ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት እየተደረገ ያለው ሩጫ በማንኛውም መመዘኛ ተቀባይነት የሌለው ተግባር ነው።'' በማለት ተግባሩ ኮንኗል።

''ይህ ሳያንስ የዜጎች ሰላም፣ ፀጥታና ደህንነት ለመጠበቅ ከተሰማራው የፀጥታ መዋቅር ጋር መጋጨትና አነሳስቶ እርምጃ እንዲውስድ መግፋት ደግሞ በፍፁም መደገም የሌለበት ተግባር ነው'' በማለት የክልሉ የኮሚኒኬሽን ቢሮ በመግለጫው አትቷል። መግለጫው በዚህ ተግባር ላይ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የተሳተፉትን አካላት በቸልታ አላልፋቸውም ብሏል።

አላማጣ ወረዳን ወክለው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል የሆኑት አቶ ረዳኢ ዝናቡ በበኩላቸው የወረዳው ነዋሪ በርካታ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ አለበት ካሉ በኋላ "በመልካም አስተዳደር እጦት ምክንያት እኛ ማንነታችን ራያ ነው፤ ስለዚህም በራሳችን ሰዎች መተዳደርና መዳኘት አለብን ማለት የጀመረ የህብረተሰብ ክፍል አለ" ብለዋል።

በትግራይ ምክር ቤት ውስጥ የወረዳው ህዝብ ተወካይ የሆኑት ወይዘሮ ጃኖ ንጉሰ ደግሞ "እኛ ትግራዋይም አማራም አይደለንም፤ እኛ ራያ ነን የሚሉም አሉ። ይህ ተግባር የፍትህ እና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ያለበትን የህብረተሰብ ክፍል ለማጋጨት እየተደረገ ያለ ነገር ነው። እንደዚህ አይነት ጥያቄ በህጋዊ መንገድ መጠየቅ አለበት።" ብለዋል።

No comments