Latest

በፌስቡክ ከመቶ አምሳ ሺህ ተከታዮች በላይ ያሏት ሕይወት እምሻው - ቢቢሲ

በፌስቡክ ከመቶ አምሳ ሺህ ተከታዮች በላይ ያሏት ሕይወት እምሻው - ቢቢሲ

ለመጀመሪያ ጊዜ በማኅበራዊ ሚዲያ 'ፖስት'ያደረግሽው


እ... ረጂም ጊዜ ነው። በዕውነት አላስታውስም፤ ስለ ሴቶች የሰውነት ቅርፅን ያልጠበቀና ቦታን ያላገናዘበ አለባበስ በተመለከተ የጻፍኩት ይመስለኛል።

በከፍተኛ ቁጥር የተወደደው 'ፖስት'

እናትና አባቴን በተመለከተ የጻፍኩት ነው። በተለይ በወቅቱ ፈር እየለቀቀ የመጣውን የዘር ፖለቲካ ይመለከት ነበር፤ እናትና አባቴ እንዴት እንደተገናኙ ከዚያም ምን ዓይነት ልጆች እንደተወለድን የጻፍኩበት ነበር። ብዙ ሰዎች ተጋርተውታል፤ ወደውታል፤ ወደ 2800 ገደማ ሰው ወዶታል።


በዝቅተኛ ደረጃ የተወደደ

(ሳቅ) በጣም ከባድ ነው!... እውነቱን ለመናገር ስንት ሰው ወደደው ብዬ አልቆጥርም። ቁጥሩን በውል ባላስታውሰውም ግን ከጋርዲያን ጋዜጣ ላይ ተርጉሜ የጻፍኩት ስላቅ ብዙ ሰው አልወደደውም፤ የስላቅና የትርጉም ሥራ ስጽፍ ብዙ ወዳጆችን አያገኝም። ፌስቡክ ላይ የሚያሳዝነው ንባብን የምንለካው በመወደድ ቁጥር ነው።

ያልተጠበቀ የውስጥ መስመር መልዕክት


ድምፃዊት ብፅአት ስዩም በውስጥ መስመር 'የምትጽፊው ጥሩ ነው' ስትለኝ ቀኑን ሙሉ ስዘል ነው የዋልኩትን (ሳቅ)፤ ደራሲ አዳም ረታም አንዲሁ ሲለኝ ደስ ይለኛል፤ አንዳንዴ የጻፉልኝን በፍሬም አድርጌ መስቀል እፈልጋለሁ።

አንድ ጊዜ ደግሞ አውስትራሊያ የሚኖር ኢትዮጵያ በጻፍኩት ታሪክ ተነክቶ አገር ቤት ለመምጣት ወሰነ። 'ኢትዮጵያ ውስጥ መጥቼ የእናቴን መቃብር ማየት እፈልጋለሁ' ብሎ ጻፈልኝ፤ አላየሁትም። በተደጋጋሚ መልዕክቶችን ልኮልኝ አላየሁትም። መጨረሻ ላይ ቢሮ እንግዳ መቀበያ ክፍል ትፈለጊያለሽ ተባልኩ።  

አንድ ጎልማሳ ሰው ቆሟል። 'የጻፍሽውን ታሪክ አንብቤ የእናቴን መቃብር ልይ ብዬ ነው የመጣሁት' አለኝ። ሽቶና ሌሎችም ስጦታዎች ይዞልኝ መጥቶ ነበር። ያልጠበቅኩት ነገር ነው የሆነው።

ፌስቡክ ሳታይ የቆየሽበት ረጅም ጊዜና ምክንያት


ባለፈው ዓመት ለ5 ወራት ለሚጠጋ ጊዜ ጠፍቼ ነበር፤ ፌስቡክ ለከት ያጣበትና የስድብና የጦርነት አውድማ የሆነበት፤ ደስ የሚል ነገር የማይገኝበት፣ የማነበው ሁሉ በአገሬ ተስፋ እንድቆርጥ የሚያደርግበት፤ የሆነ ነገር ስትጽፊ የምትወገሪበት የሆነበት ጊዜ። ያ- ነው
እጅግ አስቂኙ አስተያየት

'ሸሌ ነኝ!' የሚለውን ጽሑፍ ከለጠፍኩ በኋላ የደረሰኝ ነው( ዘለግ ያለ ሳቅ)

"ከአገር ከወጣሁ 20 ዓመታት አልፎኛል፤ ነገር ግን አዲስ አበባ ኑሮ ከባድ እንደሆነ አውቃለሁ፤ እንደዚህ ዓይነት አስቀያሚ ሥራ እንድትሠሪ ካስገደደሽ እኔ በየወሩ 200 ዶላር እየላኩ ላስተዳድርሽ እችላለሁ፤ እባክሽን ይሄን ሥራ ተይው" የሚል ነበር።

እጅግ የምትወጂው 'ፌስቡከር'


እ ... ብዙ ናቸው! ከአዳዲሶቹ አሁን በትጋት የምከተለው Derfek Fekaduን ነው።


እጅግ አወዛጋቢ 'ፖስት'

'ጨዋታው ፈረሰ' የሚል ሁለት ክፍሎች ያሉት ልብወለድ ጽፌ ነበር፤ ተከታዮቼ ታሪኩን በጨረስኩበት መንገድ ስላልተስማሙ ታሪኩን እየጨረሱ ይልኩልኝ ነበር።


ከፌስቡክ ምን አተረፍሽ?

አልከፍልበትም። የምሰማበት መድረክ ነው። በጣም ብዙ ተከታዮችን ያለምንም ልፋት ያገኘሁበት ቦታ ነው፤ ደራሲ ያደረገኝ ማኅበራዊ ሚዲያው ነው። ባለፈው ባሕር ዳር ሄጄ የማላውቃቸው 14 ሰዎች ናቸው ራት የጋበዙኝ።

በፌስቡክ ምክንያት ምን አጣሽ?

ጊዜ ይሻማል፤ አንዳንዴ ስለ አገርሽ ያለሽን አመለካከት ያንሻፍፈዋል። "አንድ ላይ ብንሆንም ተለያይተናል" የሚል ጽሑፍ ጽፌ ነበር፤ የቴክኖሎጂን መጥፎነት የሚያሳይ። ሩቅ ካሉ ሰዎች ያገናኘናል፤ ቅርብ ከሆኑ ሰዎች ያቆራርጠናል።

ከፌስቡክ ጡረታ የምትወጪበት ዘመን

ሳቅ ... አልወጣም! ሌላ የተሻለ ቴክኖሎጂ እስካልመጣ ድረስ።

በ70 ዓመትሽ 'ፖስት' የምታደርጊው?

ሃሃሃሃ ... 'ዕድሜ ደጉ!'።

ባልተጠበቀ ቦታ ምን ጻፍሽ?

ሰርግና ድግስ ላይ የሆነ ነገር እጽፋለሁ፤ አንድ ጊዜ አለሌ የነበረች ልጅ ሰርግ ላይ ተገኝቼ፤

'ኬላው ተሰበረ ኬላው ተሰበረ፣ በእናት በአባቷ ቤት ተከብሮ የኖረ' ተብሎ ሲዘፈን 'ምንም እንኳን ኬላው እንደ አቃቂ ኬላ ሥራ በዝቶበት የከረመ ቢሆንም ዘፈን ዘፈን ነውና የሰርግ ዘፈኖቻችን ዘመነኛ መሆን አለባቸው የሚል ስላቅ እዚያው ሆኜ ጽፌያለሁ።

No comments