Latest

"የፖለቲካ አስቂኙ ቀልድ ይሄ ነው" ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ



ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ

"ከሁለት ሳምንት በፊት "የምርኮ ፖለቲካ" የምትል መጣጥፍ ፅፌ ነበር። አንዳንዶች ተነጫንጨውብኝ ነበር። ተሜ ደግሞ ያን የምርኮ ፖለቲካ በሚገርም አገላለፅ አቅርቦታል። ተሜ ፊት ለፊት ነው መቼም! አንብቧት!" 

                                                                                            ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው

ግዮን፡- በትጥቅ ትግል ላይ የነበሩ ኃይሎች በድርድር መሣሪያቸውን እየጣሉ ሠላማዊ ትግልን በመቀበል ደ አገር ቤት መግባት ጀምረዋል፤ ይህንንስ እንዴት አየኸው?

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ፡- የፖለቲካ አስቂኙ ቀልድ ይሄ ነው፡፡ እየተደረገ ያለው ድርድር አይደለም፤ ለምሣሌ ግንቦት ሰባትን ብትወስደው ድርጅቱ ለአስር አመት ያህል በኤርትራ በርሃ ነበር፤ እዚህ በተለይ አዲስ አበባ ላይ ቁጥሩ የማይናቅ እጅግ በጣም በርካታ ደጋፊ አለው፡፡ 

ወያኔም በተደጋጋሚ ሣር ቅጠሉን ግንቦት ሰባት ነህ እያለ በማሰር ለግንቦት ሰባት በተዘዋዋሪ የሽያጭ ሠራተኛ ሆኖ አገልግሏል፡፡ ግንቦት ሰባት የተሻለ ጠንካራ ድርጅት ነው ብለን እናምናለን፤ ስለዚህ ይሄ ድርጅት ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ለማረፍ በያዙት የውጭ ሀገር ሆቴል ውስጥ አይደለም ተነጋግሮ መምጣት ያለበት፡፡ 

በትክክል አደራዳሪ ተመድቦ መወያየት ነበረበት፡፡ ይብዛም ይነስም በረሃ ሰብስቦ ይዟቸው የገባው ልጆች ዕድሜ ቢያንስ በአስር ዓመት ተቃጥሏል፡፡ ክሬም የሆነውን የወጣትነት ዕድሜቸውን ስለኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊያን ነጻነት ሰውተዋል፡፡ 

የእነዚህ በበረሃ የቆዩት የድርጅቱ ታጋዮች ዕድሜ አልተቃጠለም የምንለው ግንቦት ሰባት እነሱን የሚመጥን ውይይት ሳይሆን ድርድር ከመንግስት ጋር ቢያደርግ ነበር፡፡ አሁን ግንቦት ሰባት ሌላ ድርጅት ነው፤ ኢህአዴግ ሌላ ግንባር ነው፡፡ ኦነግ ሌላ ድርጅት ነው ፤ ኦህዴድ ሌላ ድርጅት ነው፡፡ 

የምር እነ ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ ለውጥ ፈላጊ ከሆኑ ድርጅቶች መጥተው በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ግንባታ ላይ አስተዋፅኦ እንዲኖራቸው አስበው ከሆነ ከእነሱ ጋር መነጋገር የፈለጉት፤ አደራዳሪ ተቀምጦ የሁሉም ድርጅት ተወካዮች ሃሳባቸውን በግልፅ አስቀምጠው ነበር የአውሮፕላን ትኬት መቁረጥ የነበረባቸው፡፡

አሁን ግን እየሆነ ያለው ያ አይደለም፡፡ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ከእስር ቤት ሲፈታ ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በቤተ መንግስት ጋብዘው አነጋግረውታል፡፡ ይሄ በሰውኛ አረዳድ ‹‹እንኳን ተፈታህ›› ለማለት እንጂ ‹‹ድርድር›› አይደለም፡፡  

አሁን አሜሪካ ውስጥ በእነ ፕ/ር ብርሃኑና ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ መሀል ተደረገ የተባለው ውይይት ነው እንጂ ‹‹ድርድር›› አይደለም፡፡ ከዚህ የተሻለ መረጃ በእናንተ በኩል ካላችሁ ልታርሙኝ ትችላላችሁ፡፡ ለፖለቲካ ፓርቲ ውይይት ዋጋ የለውም፤ ድርድር ነው ወሳኙ፡፡ 

ለምሳሌ ያህል በሀገር ውስጥና በውጭ ሲኖዶስ ነበር፣ በአቡነ ማትያስ የሚመራውና በአቡነ መርቆርዮስ የሚመራው ሲኖዶስን ያደራደረው መንግስት ነው፡፡ ወደ መንግስት ጉዳይ ስንመጣ ግን አደራዳሪውም ተደራዳሪውም የመንግስት ሰዎች ራሳቸው ናቸው፡፡

ድርጅቶች ሀገር ውስጥ ከገቡና ሠራዊቱ ከተበተነ በኋላ (ያው የሻዕቢያን አሻጥር ሳንረሳ ማለቴ ነው) አህአዴግ እኔ የምከተለው መንገድ ይሄንን ነው ቢል ምንድን ነው ዋስትናቸው? ይሄ አሳሳቢ ነው፡፡ ከ1983ቱ የኦነግ ታሪክ መማር ብልህነት ነው፡፡ 

ሠራዊቱ ካምፕ ከገባም ሆነ መሳሪያውን አውርዶ ከተበተነ በኃላ ኢህአዴግን በሚገባው ቋንቋ መልሶ ማናገር የሚቻል አይደለም፡፡ አሁንም ጌዜው አልረፈደም፡፡ ኢህአዴግ እንደ ጌታ ከሚያያቸው የምዕራብ ሀገራት አንዱ በአደራዳሪነት ቢሳተፍ ጠቃሚ ነው ብዬ አስባለሁ፡፡

ግዮን፡- ስለዚህ አካሄዳቸውና አመጣጣቸው ጥፋት ነው?
ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ፡- ጥፋት ነው ወይስ ጥፋት አይደለም የሚለውን ለድርጅቶቹ እንተወውና ድርድር ሳይሆን እንዲህ እንዲህ እናደርጋችኋለን የሚል ውይይት ነው የተካሄደው፡፡ 

‹‹ግንቦት ሰባት እኔ የመጣሁት በዚህ በዚህ ጉዳይ ተደራድሬ ነው፤ ግን አዲስ አበባ ከደረስኩ በኋላ ኢህአዴግ ክዶኛል›› ቢል ምስክር የለውም፡፡ እኔ እንዲህ ዓይነት ድርድር አላውቅም፣ ተደምረናል ከሆነ ነገሩ እሱ ሌላ ገጽታና ትርጉም ነው የሚኖረው፡፡ 

እንደዚ ከሆነ ደግሞ ለእኔ ነገርየው ‹‹መደመር›› ሳይሆን ‹መጠርነፍ› ነው፡፡

No comments