Latest

ከጠቅላይ ሚኒስትሩ መግለጫ አበይት ነጥቦች - ቢቢሲ

ከጠቅላይ ሚኒስትሩ መግለጫ አበይት ነጥቦች

ባሳለፍነው ቅዳሜ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከጋዜጠኞች ከተነሱላቸው ዘርፈ ብዙ ጥያቄዎች የሚከተሉት ዘጠኝ ዐበይት ነጥቦች ይገኙበታል።

  • የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታን በተመለከተ
የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ መዘግየት አስመልክቶ ለቀረበላቸው ጥያቄ ግድቡ የዘገየበት ምክንያቶች ሁለት ናቸው ብለዋል።

የመጀመሪያው ከፕሮጀክቱ አስተዳደር ጋር የሚያያዝ ነው ያሉ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ከፕሮጀክቱ ዲዛይን ጋር እንደሚገናኝ ተናግረዋል።

ከልምድ ማነስ እና ከሥራ ባህላችን ጋር ተያይዞ እንደ ህዳሴ ግድቡ ዓይነት ግዙፍ ፕሮጀክቶችን በተያዘላቸው የጊዜ ገደብ ማጠናቀቅ አልቻልንም ብለዋል።

አብዛኛው የግንባታውን ሥራ ይሠራ የነበረው የመከላከያ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ፍላጎት እንጂ አቅም እንዳልነበረው ገልፀዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሜቴክ ውስጥ የነበረውን ፍላጎት የሚደግፍ ዕውቀት የለም ብለዋል።

ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ ግድቡን ለመጎበኘት ወደ ግንባታ ሥፍራው እንደሄዱ ያስታወሱት ጠቅላይ ሚንስትሩ፤ የባለሙያዎች ቡድን አዋቅረው የግድቡን የግንባታ ሂደት እንዲፈተሽ እንደተደረገም ተናግረዋል።

በባለሙያዎቹ ሪፖርት መሠረትም ሜቴክ ይሠራቸው የነበሩ ሥራዎች ተወስደው ልምድ ላላቸው ሌሎች ድርጅቶች አሳልፎ እንዲሰጥ፤ ያ ካልሆነ ግን ግንባታውን ለመጨረስ ከዚህ በላይ በርካታ ዓመታት ያስፈልገዋል ብለዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ አያይዘውም ይህ ሐሳብ ኢንጂነር ስመኘውም የሚስማማበት ነበር ብለዋል።
  • ወቅታዊ መረጃዎች ለሕዝብ እየደረሱ አይደለም።
የሰኔ 16ቱ የቦምብ ጥቃት እና ከኢንጂነር ስመኘው አሟሟት ጋር በተያያዘ መረጃዎች በፍጥነት ለሕዝብ አልደረሱም፤ የሚወጡትም መረጃዎች ለተወሰኑ መገናኛ ብዙኃን ብቻ ነው የሚሰጡት የሚሉ ቅሬታዎች ተነስተዋል።

ጠቅላይ ሚንስትሩም መረጃዎች ሳይጣሩ ለሕዝቡ ማቅረቡ የራሱ የሆነ አደጋ ስላለው ነው መረጃዎችን በፍጥነት ከመስጠት የተቆጠብነው ያሉ ሲሆን፣ ምርመራው ጊዜ የሚወስድ መሆኑንም ጨምረው አስታውሰዋል።

''የኛም የምርመራ ተቋማት የአቅም ውስንነት አለባቸው። የኢንጂነር ስመኘው ሞትን በተመለከተ እና ከ16ቱ ፍንዳታ ጋር ምረመራ እያካሄዱ የሚገኙት ተቋማት በቅርቡ መግለጫ ይሰጣሉ።'' ብለዋል።
  • በመቀሌ በቁጥጥር ሥር ዋሉ ስለተባሉት የፌደራል ፖሊስ አባላት
ጠቅላይ ሚንስትሩ የፌደራል ፖሊስ አባላት በመቀሌ አየር ማረፊያ አቅራቢያ በቁጥጥር ሥር ውለዋል የሚለው መረጃ የተሟላ እና ትክክለኛ አይደለም ብለዋል። ጠቅላይ ሚንስትሩ ''የፌደራል ፖሊስ አባላት የሆኑ ወደ መቀሌ ተጉዘው ነበር፤ ይሁን እንጂ የክልሉ ባለሥልጣናት መረጃው ስላልነበራቸው ከየት መጡ የሚል ጥያቄ አነሱ እንጂ የታገተ ኃይል አልነበረም'' ብለዋል።

የፌደራል ፖሊስ አባላቱ የሄዱበትን ሥራ አጠናቀው ተመልሰዋል ብለዋል። ጠቅላይ ሚንስትሩ ጨምረውም አሁንም ቢሆን በርካታ የፌደራል ፖሊስ አባላት በትግራይ ይገኛሉ።

የመቀሌ ዩኒቨርሲቲ እንዲሁም አየር ማረፊያን ለመሳሰሉ ተቋማት ጥበቃ እያደረጉ ነው ሲሉ ተናግረዋል።
  • የኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማርያም ይቅርታ
ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማርያምን በማስመልከት ''በሕገ-መንግሥቱ መሠረት የምሕረት አዋጁ የቀይ ሽብር ጉዳይ እንደማይካተት በግልጽ አስፈሯል።

ስለዚህ ኮሎኔል መንግሥቱ በይቅርታ ወደዚህ ሊመጡ አይችሉም'' ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ መልስ ሰጥተውበታል።
  • የአማራ ክልል እና የሱዳን ድንበር ጉዳይ
በአማራ ክልል እና የሱዳን ድንበር አዋሳኞች ላይ በተደጋጋሚ ግጭቶች እየተከሰቱ ጉዳት እየደረሰ ነው።

ለዚህ ችግር ዘላቂ መፍትሄ ለመስጠት ምን ታስቧል የሚል ጥያቄ ከጋዜጠኞች ቀርቦላቸው ነበር።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጉዳዩ ላይ በሰጡት ምላሽ ለረዥም ጊዜ ኢትዮጵያ እና የሱዳን የድንበር ወሰን መልክ አልያዘም ብለዋል።

በቅርብ ጊዜ በመሪዎች ደረጃ እና በኮሚሽን ደረጃ ውይይት ተደርጎ የሁለቱም ወገን የታጠቁ ኃይሎች እንዲለቁ እና ጥበቃን በሚመለከት ደግሞ ከሁለቱም ወገን የተውጣጡ ኃይሎች ጥበቃ እንዲደረግ ተስማምተናል ብለዋል። 


ይሁን እንጂ አሁንም የይገባኛል ጥያቄ በሁለቱም ወገን እንደሚነሳ ጠቅላይ ሚንስትሩ ያስታወሱ ሲሆን ይህን ለመፍታት ጊዜ የሚወስድ ስለሆነ ወደ ፊት ጊዜ ወስደን የምንፈታው እንደሆነ ተደርጎ ቢታሰብ ጥሩ ነው ብለዋል።
  • ኦሮሚያ የፌደራል የሥራ ቋንቋ ስለማድረግ
ጥያቄው መነሳቱ በቀና ዓይን ነው የማየው ያሉት ጠቅላይ ሚንስትሩ፤ ኦሮሞው ኦሮሚኛ የፌደራል የሥራ ቋንቋ ይሁንልኝ ማለቱ ኢትዮጵያ ሃገሬ ናት የሚል ስሜት ስላለው ነው። ይህም ያስደስተኛል ብለዋል።  

ጠቅላይ ሚንስትሩ ከአንድ በላይ ቋንቋ መጠቀማችን መልካም ነገር ነው ያሉ ሲሆን ኦሮምኛን የፌደራል ቋንቋ ለማድረግ ግን የሕግ-መንግሥት ማሻሻያ ያስፈልገዋል በማለት ጥያቄው ተግባራዊ ከመደረጉ በፊት ጊዜ ሊወስድ እንደሚችል ጠቁመው አልፈዋል።
  • ወደ ሃገር ውስጥ የገቡ የታጠቁ ኃይሎችን በተመለከተ
መንግሥት ያደረገውን ጥሪ ተከትሎ የተለያዩ የታጠቁ ኃይሎች ወደ ሃገር መግባታቸውን ይታወሳል። በዚህም የታጠቁ ኃይሎች ጦር መሣሪያ አንግበው ሲንቀሳቀሱ ይታያል። እነዚህ ኃይሎች እንደታጠቁ ይቆያሉ ወይ የሚል ጥያቄ ቀርቦላቸው ነበር።

''የታጠቁ ኃይላቸው ከነትጥቃቸው የሚቆዩ ከሆነ ለምን ይመጣሉ?'' ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ መልሰው የጠየቁ ሲሆን፤ ''የያዝነው መርህ ትጥቅ አያስፈልግም፤ ክላሽ ይዘው የሚቀጥሉ ከሆነ መምጣቱ ዋጋ የለውም'' ብለዋል።
  • ኢትዮጵያዊነትን እንዴት ይገልጹታል
ጠቅላይ ሚንስትሩ ኢትዮጵያዊነትን የምገልጸው ኢትዮጵያዊ በመሆን ነው ብለዋል። ''ኢትዮጲያዊነት ጥልቅ ስሜት ነው። ኢትዮጵያዊነትን ኢትዮጵያዊ በመሆን ብቻ ነው የሚገለጸው። በእኔ እምነት አቃፊነት ነው ብዬ አስባለሁ።'' ብለዋል።
  • ጠቅላይ ሚኒስትሩ መልስ ያልሰጡበት ጥያቄ
የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ሥርዓተ መንግሥት የፓርላማ ስርዓት ያለው መሆኑ ይታወቃል። ሆኖም ከጋዜጠኞች የመንግሥቱን ሥርዓት ከፓርላማ ስርዓት ወደ ፕሬዚዳንታዊ ለመቀየር ሐሳብ አለዎት ወይ የሚል ጥያቄ ቀርቦላቸው ነበር። ይሁን እንጂ ጠቅላይ ሚንስትሩ ለጥያቄው ምላሽ አልሰጡም።

No comments