Latest

የብአዴን መግለጫ፡- ከስያሜ መቀየር እስከ ኢትዮ ሱዳን ድንበር - ቢቢሲ



የብአዴን መግለጫ

የብሄረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን) በ12ኛ መደበኛ ድርጅታዊ ጉባኤው የተለያዩ ውሳኔዎችን አስተላልፏል።

ነሃሴ 17 እና 18 /2010 የተደረገውን ስብሰባ ተከትሎ ድርጅቱ በኦፊሳላዊ ገፁ በክልሉ ያለውን ወቅታዊ መንፈስ «ወሳኝና ታሪካዊ » ሲል የገለፀው ሲሆን ይሄን ታሳቢ ያደረጉ ባለ 12 ነጥብ ውሳኔዎችን ማስተላለፉን አትቷል።

በውሳኔዎቹ ድርጅቱ ፣

  • የስያሜ፣ የፖለቲካ ፕሮግራም እና መተዳደሪያ ደምብ ማሻሻያ እንደሚያደርግ ይፋ አድርጓል፤

  • የጥረት ኮርፖሬት እና የአማራ ብድርና ቁጠባ ተቋም (አብቁተ) የተባሉት የልማት ድርጅቶች ተጠሪነታቸው ለክልሉ መንግስት እንዲሆን ፖለቲካዊ ውሳኔ አስተላልፏል፤

  • ቀደም ብሎ የተደረገውን በኢትዮጵያ እና ሱዳን መካከል ያለውን የድንበር ማካለል በተመለከተ የተገባውን ስምምነት «መብታችንን ያላስጠበቀ፣ የሚመለከታቸውን አካላት ያላሳተፈና የጋራ አቋምም ያልተያዘበት ውሳኔ » ሲል ከተቸው በኋላ፤ ውሳኔው በፌዴራል መንግስት በኩል አስቸኳይ ማስተካከያ እንዲደረግበት ጠይቋል።

በተጨማሪም የሱዳን ጦር ያለአግባብ ሰፍሮበታል ካለው በቋራ ወረዳ ከሚገኘው ነፍስ ገበያ ከተባለው ስፍራ ለቆ እንዲወጣ የፌዴራል መንግስትም ይሄንን እንዲያስፈፅም ጠይቋል።
  • ከእነዚህ ውሳኔዎች በተጨማሪ የግለሰብ እና የቡድን መብት ተጣጥመው እንዲጓዙ እንደሚተጋ፣ በስደት ቆይተው ከተመለሱ «ተፎካካሪ ፓርቲዎች» ጋር ተከባብሮ ለመስራት እና ዲሞክራሲን ለማስፋት ፅኑ ፍላጎት እንዳለው አስታውቋል።


  • «የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ መንግስት አባላት የሆኑ ክልሎች አከላለል በህዝቦች እውነተኛ ፍላጎትና ንቁ ተሳትፎ፣ ብዝሃነትንና ሃገራዊ አንድነትን በሚያጠናክር አግባብ ሕገ መንግስቱን መሰረት አድርጎ እንዲከለል እንታገላለን፡፡» በማለትም አክሏል።
የብአዴን ማእከላዊ ኮሚቴ አቶ በረከት ስምኦንን እና አቶ ታደሰ ካሳን ከማእከላዊ ኮሚቴ አባልነት ማገዱም ይታወሳል።

የአቶ በረከት እና የአቶ ታደሰ እገዳ "በጥረት ኮርፖሬት ላይ ከሰሩት ጥፋት ጋር የተያያዘ ነው" ተብሏል። ስለዚህም እስከ ቀጣዩ የብአዴን ማእከላዊ ኮሚቴ መደበኛ ጉባኤ ድረስ ከኮሚቴው አባልነት ተግደው ይቆያሉ ተብሏል።

No comments