Latest

«ወይዘሮ አና ጎሜዝ፤ እርስዎ አያገባዎትም! አርፈው ይቀመጡ በልልኝ» በረከት ስምኦን (ቢቢሲ)

በረከት ስምኦን

ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት በኢትዮጵያ ፖለቲካ ከፍተኛ ተጽእኖ ፈጣሪ የነበሩት አቶ በረከት ስምኦን በቅርቡ ከብአዴን ማእከላዊ ኮሚቴ አባልነት መታገዳቸው ይታወሳል።

አቶ በርከት የብአዴን ውሳኔን በተመለከተ እና የወደፊት የፖለቲካ ህይወታቸው ምን ሊሆን እንደሚችል ለቢቢሲ አጋርተዋል።

ጥያቄ፦ የታገዱባቸውን ምክንያቶች ያምኑባቸዋል?
አቶ በረከት፦ አላምንባቸውም። ምክንያቱም ሁለቱም [ክሶች] መሠረተ ቢስ ናቸው። የአማራ ሕዝብን አይጠቅሙም። የለውጥ ኃይሎች አይደሉም። ጥረትንም ችግር ፈጥረውበታል ነው የሚሉት። ሁሉም መሠረተ ቢስ ናቸው።

ለአማራ ሕዝብ አይጠቅሙም የሚለው እኛ ዕድሜ ልካችንን ለራሳችን ሳናስብ በአማራ ክልል ነው ስንታገል የኖርነው። 'ክልሉ ተለውጧል፤ አድጓል፤ ተሻሽሏል፤ ባለፉት 25 ዓመታት ወደፊት ተራምዷል'፥ ሲሉ የነበሩ ሰዎች ይህን [ለውጥ] ወይ ብቻችን አምጥተነዋል ማለት አለባቸው፥ ወይ ደግሞ አብረን ነው ያመጣነው ማለት አለባቸው።

የለውጥ ኃይሎች አይደሉም የተባለውም መሠረተ ቢስ ነው። ሰው አሁን ነው ድምጹ መሰማት የጀመረው።

አሁን ሦስት አራት አምስት ወራት። እኛ ከ2002 ጀምሮ "በከባድ ሁኔታ ችግር ላይ ነን፤ ድክመታችን በዝቷል፤ አገሪቱንም ወደ ቀውስ የሚያመሩ ነገሮች ተበራክተዋል፤ መሻሻል አለብን' ብለን የለውጥ ሐሳቡን ያመጣነው እኛ ነን።

ለዚህም ከባድ ዋጋ ክፈለናል። ያልከፈልነው ነገር የለም። የለውጥ ኃይሎች አይደሉም የሚባለው፥ የለውጥ ጀማሪዎች ቀስቃሾች እኛ ነን። ግን ወጥተን እንዲህ አድርገናል ማለት አልወደድንም።

ጥረትን በተመለከተ ለመነሻ የተሰጠን ገንዘብ 20 ሚሊዮን እና 31 ያረጁ ኤንትሬዎች ማርቼዲሶች ከጦርነቱ የተራረፉ ናቸው።

አሁን 11 ቢሊዮን ብር የሚያወጡ 20 ኩባንያዎች ለአማራ ክልል አስረክበናል። ከምስጋና ጋር ሊሸኙን ይገባ ነበር። ጽድቆ ቀርቶ በወጉ በኮነንኝ አንዲሉ በወጉ እንኳ አላሳናበቱንም።

ኦዲትን ሪፖርት አለን። ሁሉም ነገር አለን። በኢትዮጵያ ውስጥ ኢንዶውመንት ተብሎ የግብር ከፋይ ምሳሌ ይጠቀስ ቢባል ጥረትን ያክል ግብር ከፋይ ተምሳሌት የሆነ ድርጅት የለም። ስለዚህ በዚህ ደረጃ ያነሱትም ነገር መሠረተ ቢስ ነው።

ጥያቄ፦ ከማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባ የቀራችሁበት ምክንያት ምንድነው?
አቶ በረከት፦ ሁለታችንም ጥሪው ደርሶናል። እኔ ደርሶኛል፤ ታደሰ ኢሜሉ ስለተዘጋ አልደረሰውም። የጥረት ኢሜሉ ነው የነበረው፤ [እሱም] ተዘግተቷል።

እኔ እንደደረሰኝ ዐይቼ ምን እናድርግ ተባባልን። ብንሳተፍ ጥሩ ነበር፤ ግን ክልሉ ውስጥ የሚካሄደው ስብሰባ የጸጥታ አስተማማኝነት በሌለበት ሁኔታ ነው የሚካሄደው፤ ስለዚህ እንንገራቸው ተባባልን።

ጠየቅን እነሱም ችግር አለ፤ የጸጥታ ዋስትና ግን አንሰጣችሁም አሉ። ስለዚህ ልንሳተፍ አንችልም። የኛ ችግር አይደለም።

ጥያቄ፦ እርስዎ አሉበት በተባለ ሆቴል ጥቃት ተሰንዝሮ ነበር፤ ከዚያም በኋላ በደቦ የሚፈጸም ሕገወጥነት የሚመስል ነገር በክልሉ ይስተዋላል። ይህን የመሰሉ ጥቃቶች ብአዴን ማስቆም ለምን አቃተው?
አቶ በረከት፦ ብአዴን በሕዝብ ተመርጦ ክልሉን እያስተዳደረ ያለ ድርጅት ነው። መንግሥት የመሠረተው እሱ ነው።

መንግሥት ባለበት አገር የሕግ የበላይነት ሊከበር አልቻለም። ሥርዓት አልበኝነት በየቦታው አለ። ይሄ እኔን ብቻ የሚመለከት አይደለም። ብዙ ሰው ለአደጋ የተጋለጠበት ሁኔታ ነው ያለው።

ረዘም ላለ ዓመታት ማንነቱ ያልታወቀ ኃይል ሱቅ ዝጉ ይላል፣ ያዘጋል፤ ክፈቱ ይላል፣ ያስከፍታል። መንገድ ዝጉ ይላል፣ ያዘጋል። መንገድ ክፈቱ ይላል፣ ያስከፍታል።

[ብአዴን] በክልሉ ውስጥ ሕግና ሥርዓት የሚያስከብር በዚያ ደረጃ አቅሙ ተጠናክሮ የሚገኝ መንግሥት ሆኖ አይታየኝም።

ጥያቄ፦ ማንን ተጠያቂ ያደርጋሉ ታዲያ?

አቶ በረከት፦ ዞሮ ዞሮ አመራሩ ነዋ። የአገራዊ ሕገ መንግስቱም የክልላዊ መንግሥቱም የማስተዳደር ኃይል ይሸከማል። እርቀ ሰላም ሊኖር ይችላል።

መታረቅ መጥፎ ነው የሚል አቋም የለኝም። ግን ሥርዓት አልበኝነት መስፈን አለበት ማለት አይደለም። ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ደጋግመው 'ዲሞክራሲን ነጻነትን ስንፈልግ ሕግና ሥርዓት እየጣስን አይደለም' ብለው አስቀምጠዋል። ይሄ ነው ትክክለኛው መልስ።

በክልሉ ይሄን መርህ የሚያረጋግጥ ነገር አይደለም የማየው።

ጥያቄ፦ ቀደም ሲል ራስዎን አግልለው ነው በድጋሚ የተመለሱት። አሁን ይቆጮታል። ያኔ እንደወጣሁ በቀረሁ ኖሮ በሚል?
አቶ በረከት፦ በአቶ ኃይለማርያም ጊዜ ነው ጥያቄ ያቀረብኩት። በአካሄዱ ብዙ አልተስማማሁም። ብዙ ጥፋት ይፈጸም ነበር። በዛው ውስጥ አብሮ መቀጠል የማልችለበት ሁኔታ እየተበራከተ ሲመጣ ጥያቄ አቅርቢያለሁ።


በመጨረሻ ደግሞ ነባሮች ተሳተፉ ተብለን ስንሳተፍና በኛም አስተዋጽኦ ጭምር የለውጥ እንቅስቃሴ ሲጀመር አብረን እንቀጥል ተባለ፤ አብረን እንቀጥላለን አልን።

የራሱ ጉዳይ ብለህ ጥለከው የምትሄደው ነገር አይደለም።፥ በዙ መስዋእትነት ስለተከፈለበት። የብአዴን ማእከላዊ ኮሚቴም የካቲት ላይ 'እባክህ ተመለስ' ብሎ 'በቃ እኛን ጥለህ የት ትሄዳለህ' ብለውኝ ነው የተመለስኩት።

አሁን 6 ወር ባልሞላ ጊዜ በሌለንበት የለውጥ ኃይል አይደለህም ብለው ተባረሀል ብለውኛል ወይ አግደውኛል። የካቲት ላይ በተካሄደ ስብሰባ 'እባክህን በቃ ደስ እንዲለን ተመለስ' ብለውኝ እንጂ እኔ ይበቃኛል ብዬ ነበር።

ጥያቄ፦ ለምን ይመስልዎታል እንደዚህ ዓይነት ውሳኔ የተላለፈብዎ?
አቶ በረከት፦ የኛ ክልል አይደሉም ብለው የሚያስቧቸውን ሰዎች ማጥቃት፤ በዚያ መልክ የተያዘ አለ። ተሳስታችኋል አትሠሩም ስንፍና አለባችሁ ብለን ወቀሳ ያቀረብንባቸው ሰዎች ይቀየማሉ።

ሦስተኛ ብልሽት አለ የሚልዋቸውን ሰዎች፣ በራሳቸው እምነት በነጻነት ቆመው የሚናገሩ ሰዎችን አለመውደድ አለ። እነዚህን ሰዎች ነው እየተበቀሉ ያሉት። ይሄ በጣም አደገኛ ነው።

ጥያቄ፦ ወይዘሮ አና ጎሜዝ በትዊተር ገጻቸው ላይ ስለሰጡት አስተያየት ምን ምላሸ ይሰጣሉ?
አቶ በረከት፦ ወይዘሮ አና ጎሜዝ ፖርቹጋላዊት ናቸው። ፖርቹጋል የአውሮፓ አፍሪካ ነው የምትባለው። በደንብ ካልለሙት አገሮች አንዷ ናት።

ሴትየው በቁም ነገር የሚያስቡ ከሆነ ስለ ፖርቹጋል ቢያስቡ፤ ጊዜያቸውን የአገራቸውን ችግር በመፍታት ቢያውሉት። ኢትዮጵያ ሉአላዊት አገር ናት።

ሿሚ ሻሪ የአገሬው ሕዝብ ነው። 'እርስዎን አያገባዎትም። አርፈው ይቀመጡ። ፖርቹጋልን ቢያግዙ ይሻሎታል' በልልኝ። ይሄ በሉአላዊት አገር ጣልቃ መግባት የድሮ የፖርቹጋል የቅኝ አገዛዝ አስተሳሰብ አለቀቃቸውም።

ጥያቄ፦ ከፖለቲካ ራስዎን አገለሉ ማለት ነው?
አቶ በረከት ፦ በፖለቲካ መተካካት ሂደት አያት ሆነናል። የኛን ትውልድ አመራር እንደ አያት ብትወስድ፥ የአቶ ኃይለማርያምን እንደ አባት፤ የዐብይን እንደ ልጅ ብትወስድ አያት ሆነናል።

እንደ አያት ራቅ ብለህ ተረት የምታወራብት ጊዜ ላይ ነው ያለነው። ተረት ለማውራት ፖለቲከኛ መሆን አይጠይቅም።

ጥያቄ፦ በዋናነት ምን ላይ ይሳተፋሉ ከዚህ በኋላ?
አቶ በረከት፦ አሁን እንኳ ባለው ሁኔታ ከልጆቼ ጋር ቤቴ ውስጥ ቁጭ ብዬ መጽሐፎቼ ጋር እየተጫወትኩ ማለፍ ነው የምፈልገው።

ጥቃቱ ስለተደጋገመብኝ ብቻ ነው እንጂ… ከሚዲያም ከሁሉም ነገር ርቄ ታጥቤ ተለቃልቄ መኖር ነው የምፈልገው።

No comments