Latest

ዶክተር አብይ ቃሉን በልቷል፣ ለአማራው ከትህነግ አልተለየም! ጌታቸው ሺፈራው - ክፍል 2


ዶክተር አብይ አህመድ ወደ ስልጣን የመጣው "ከድሮው የኢህአዴ የተለየ አሰራርና አመለካከት" በሚል ቅስቀሳው ነው። ከትህነግ/ህወሓት የተለየ አሰራር ይከተላል ያሉ አካላትም ሞቅ ያለ አቀባበል አድርገውለታል። ትህነግ/ኢህአዴግ በአድርባይነታቸው የታወቁትን ሰዎች በሕዝብ ላይ እየሾመ፣ እነዚህን አድርባይና ፈሪ ባለስልጣባት ከስራቸው በሚገኝ ተራ ፖለቲከኞች እየሾረ ስልጣኑን አስቀጥሏል።

ከዚህም አለፍ ሲል በሕዝብ ላይ ጥላቻ ያላቸውን አመራሮች በመሾም ስልጣኑን ሲያስቀጥል ቆይቷል። ዶክተር አብይ አህመድ እነዚህን አድርባይና ከህዝብ ጥቅም በተፃራሪ የቆሙ አመራሮች እየተጠቀመ ስልጣን ላይ ከቆየው ትህነግ/ኢህአዴግ የተለየ ሀሳብና አሰራር እንደሚኖረው በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ እየቀሰቀሰ በሕዝብ ተቀባይነት አትርፏል። ሆኖም ወደ ስልጣን ያመጣቸው ሰዎች ከዚህ ቅስቀሳ የተለየና የድሮውን አሰራር ያስቀጠሉ ሆነው እናገኛቸዋለን። ለምሳሌ ትህነግ/ህወሓት ሲያደርግ የነበረውን በአማራው ላይ ማስቀጠሉን በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል። ለምሳሌ:_

1) ጀኔራል አደም መሃመድ: ብሔራዊ መረጃ ደሕንነት አገልግሎት

ይህን ሰው የጌታቸው አሰፋን ቦታ ሰጥቶታል። ይህ ቦታ የተሰጠው ግን ለሕዝብ ባለፈው ፍቅር አይደለም። በብቃቱ አይደለም። ትህነግ/ህወሓት ይህን ሰው በአድርባይነቱና በአማራ ሕዝብ ላይ ባለው ጥላቻ ሾሞ መጠቀሚያ ሲያደርገው ቆይቷል። አማራው ላይ ጥቃት እየተፈፀመ ዝም ከማለቱ ባሻገር፣ አንተ ነፍጠኛ እያለ አማሮችን የሚያወግዝ ሰው ነው። 

በ2010 ዓም የተደረገውን የሰሜን ወሎ ተቃውሞን ለመቀልበስ በሄሊኮፍተር የታገዘ ጥቃት እንዲደረግ የእሱ አስተዋፅኦ አለበት። የህወሓትን የበላይነት ለማስጠበቅ የትኛውንም መስዋትነት የሚከፍል ሰው ነው። ወንድሙ በመፈንቅለ መንግስት ተጠርጥሮ ለ9 አመት ሲታሰር ትህነግን ፈርቶ አንድ ቀን አልጠየቀውም። ቤተሰቡን አልጠየቀም። ለወንድሙ ያልሆነ ለሕዝብ ሊሆን አይችልም።

2) ሌ/ጀኔራል ሀሰን ኢብራሂም: መከላከያ መረጃ መምርያ

ይህ ሰው መከላከያ ሰራዊቱ ውስጥ የመረጃ ክፍል ሆኖ አገልግሏል። ወደሰራዊቱ የገባው በ1984 ሲሆን የረባ የውጊያ ታሪክ ሳይኖረው ጀኔራልነት ማዕረግ ሰጥተውታል። አማራ ጠል የሆነው የአብርሃ ወልደማርያም (ኳርተር) መረጃ ሲሆን የአማራ ጀኔራሎች ከሰራዊቱ እንዲገፉ በማድረግ እጁ አለበት። 

በመፈንቅለ መንግስት የተከሰሱትን ጨምሮ በርካታ አማራ የሰራዊት አባላትን ለትህነግ አሳልፎ የሰጠ ሰው ነው። ሻለቃ ምስጋናው እና ሻለቃ አዱኛ የተባሉ በማንነታቸው የታሰሩት የአማራ ተወላጆችን የመረመረ እሱ ሲሆን ጀኔራል ኃይሌ ጥላሁን እና ጀኔራል ተፈራ ማሞ መለስን ለማስገደል እየሰሩ ነው ብላችሁ መስክርባቸው ብሎ የሀሰት ምስክር አድርጎ ሊያቀርብባቸው ነበር።

ዶክተር አብይ አህመድ በእነ መለስ ዘመን ትህነግ አማራን አሳልፎ መስጠቱ እንደ ትልቅ ነገር ተቆጥሮለት የቆየውን ሰው የመከላከያ ሰራዊት መረጃ መምርያ ሀላፊ አድርጎ ሾሞታል።

3) ይናገር ደሴ: የብሔራዊ ገዥ

ይናገር ደሴ በአድርባይነታቸው ከሚታወቁት የብአዴን ባለስልጣናት መካከል አንዱ ነው። ከአማራ ሕዝብ ጥቅም ይልቅ የግሉን ጥቅም የሚያጋብስ፣ አድርባይ ሰው መሆኑን አብረውት የሰሩት ይመሰክራሉ። በአንድ ወቅት የአማራ ክልል ፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት ቢሮ ኃላፊ የነበረው የአሁኑ የብሔራዊ ባንክ ገዥ የክልሉን በጀት ቆልፎ የግሉን ጥቅም ለማግኘት ወደ ውጭ ሄዷል። 

የትምህርት እድል ያገኘው ይናገር "ከአሁን በኋላ ገንዘብ እንዳይወጣ" ብሎ ለባንኮች በፊርማው ፅፎ ለትምህርት ሄዷል። ገንዘብ ሲፈለግ ባንኮች አንሰጥም አለ። የይናገር ደሴን ፊርማ አሳይተው። ይህ ሰው ቢያንስ እሱን ወክሎ የሚሰራ ሰው ማስቀመጥ ነበረበት። በሂደት ሌላ ሰው ይተካ ነበር። ነገር ግን ሰውዬው ይናገር ደሴ ነው። ለሕዝብ ግድ የሌለው ይናገር!
ይናገር ደሴ ጊዜ የሰጠውና ሀይል ያለው የሚያሽከረክረው፣የሕዝብ ጥቅም ግድ የማይሰጠው ሰው ነው። ይህም እንደ ብቃት ተቆጥሮለት የብሔራዊ ባንክ ገዥ ተደርጓል።

4) ተመስገን ጥሩነህ: የኢንፎንሜርሜሽን መረብ ደሕንነት ኤጀንሲ (ኢመደኤ) ዳይሬክተር

አቶ ተመስገን ጥሩነህ ዶክተር አብይ አህመድ ይሰራበት የነበረው ኢመድኤ (INSA_ኢመድኤ ከብሔራዊ ደሕንነት መስርያ ቤቱ ይለያል) ይሰራ ነበር። የትህነግ/ህወሓት አባላት በሞሉበት በዚህ መስርያ ቤት ተመስገን ደፍሮ የማይናገር፣ ለትህነግ/ህወሓት ሰዎች ምቹ የነበር ሰው ነው። ከዶክተር አብይ አህመድ ስር እያለ ታዛዥ ስለነበር እንደ ብቃት ተቆጥሮ ዋና ዳይሬክተር አድርጎታል።

5) ጥላዬ ጌቴ: ትምህርት ሚኒስትር

ጥላዬ ጌቴ የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ ሀላፊ የነበረ ሰው ነው። በዚህን ወቅት በተሰራው ፀረ ሕዝብ ስራ የቀደሙት ትምህርት ቤቶችም ፈርሰው ተማሪዎች በዳስ እንዲማሩ ተገድደዋል። በአማራ ክልል ላለው የወቅቱ የትምህርት ውድቀት ቀዳሚ ተጠያቂ ከሆኑት ሰዎች መካከል ጥላዬ ጌቴ ቀዳሚው ነው። ፈሪና አድርባይ ከመሆኑ ባሻገር ለሕዝብ ደንታ የሌለው ሰው ነው። ይህ እንደብቃት ተቆጥሮለት ከፍ ያለ ስልጣን ተሰጥቶታል። ይህን ሰው በዶክተር አብይ ስልጣንም የትምህርት ሚኒስትር ሆኖ ቀጥሏል።

6) ከበደ ጫኔ: የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር

ይህ ሰው ስልጣን ላይ የቆየው አማራውን ለትህነግ በማስገዛት ፍላጎቱ ነው። በሕዝብ ካለው ጥላቻ አንፃር በስልጣን ላይ ያለው በረከት ማለት ከበደ ጫኔ ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም። በቅርቡ የተለቀቀውን ቪዲዮ የተመለከተ ከበደ ጫኔ የሚባል ሰው አማራን ወክሎ ተቀመጠ ሲባል አላማውን ምን እንደሆነ ይገባዋል። ይህ ሰው ፀረ አማራ በመሆኑ ስልጣን ላይ እንደቆየ ሁሉ በአብይ ዘመን ደግሞ ሚኒስይር ቦታ ላይ ሆኖ ቀጥሏል።

7) አህመድ አብተው: የፖሊሲ ጥናትና ምርመር

አህመድ አብተው ትህነግ/ህወሓት የሚፈልገው አድርባይነት "ብቃት" ተደርጎለት ስልጣን ላይ የቆየ፣ አሁንም በአብይ ዘመን ዳይሬክተር ሆኖ የተሾመ ሰው ነው።

ከላይ የተጠቀሱት ግለሰቦች እንደምሳሌ ተጠቀሱ እንጅ በየቦታው ትህነግ/ህወሓት በአድርባይነታቸው፣ በታዛዥነታቸው፣ ከዚህ አለፍ ሲል ደግሞ ፀረ አማራ ስለሆኑ ሲጠቀምባቸው የነበሩትን ሰዎች ዶክተር አብይ ከፍተኛ ስልጣን ሰጥቷቸዋል። በእነዚህ ቦታ የሚቀመጥ ሰው ጠፍቶ አይደለም። ለአብነት ያክል ከእነ ጀኔራል ሀሰን የተሻሉ ከ5 በላይ ጀኔራሎች አሉ።

ዶክተር አብይ ወደ ስልጣን ሲመጣም ሆነ ስልጣን ከያዘ በኋላ የሕዝብን ጥቅም የሚያስጠብቁ ሰዎችን እንደሚመርጥ ሲጠቁም ቆይቷል። የሆነው ግን በተቃራኒው ነው ፀረ ሕዝብ የሆኑትን ትህነግ/ህወሓት ሰጥቷቸው ከነበረው ስልጣን በላይ ከፍ አድርጓቸዋል። ልዩነቱ ድሮ ከነበራቸው የተሻለ ስልጣን ማግኘታቸው ነው። አሁንም ፀረ ሕዝብ ናቸው። ፀረ ሕዝብ ያልሆኑት አድርባይ ናቸው። 

ሌሎቹ ደግሞ ታዛዥ ናቸው። እነዚህን እንደማይመርጥ ይጠቁም የነበረው ዶክተር አብይ በእውኑ ግን ትልቅ ስልጣን ሰጥቷቸዋል። ስለሚታዘዙት ነው፣ ለሕዝብ ጥቅም ስለማይቆሙ ነው! በመሆኑም ዶክተር አብይ በትህነግ/ህወሓት ዘመን ድክመታቸው እንደ ጥንካሬ ተቆጥሮላቸው ስልጣን ላይ የቆዩትን፣ ይበልጡን ከፍ ሲያደርግ ከድሮው ትህነግ/ኢህአዴግ የተለየ ሀሳብና አመለካከት ይዞ እንደሚመጣ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የቀሰቀሰውን ስቷል። ቃሉን በልቷል።

ዶክተር አብይ የኢህአዴግ ሊቀመንበር ነው፣ የኢህአዴግ ሊቀመንበር ሆኖም ከድሮው የተሻለ (አድርባይነትን፣ ታዛዥነትን፣ ፀረ ሕዝብነትን እንደብቃት መጠቀምን) የተለየ አመለካከት ያመጣል ብለው ላመኑበት ቃሉን በልቷል።

No comments