Latest

ሜቴክ ወታደራዊ ቁሳቁስ የሚያመርትበትን ዘርፍ ሊነጠቅ ነው - ቢቢኤን

ሜቴክ ወታደራዊ ቁሳቁስ የሚያመርትበትን

የብረታ ብረት እና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን (ሜቴክ) ወታደራዊ ቁሳቁስ የሚያመርትበትን የኢንዱስትሪ ዘርፍ ሊነጠቅ ነው፡፡  


ድርጅቱ ቀደም ሲል የተለያዩ ወታደራዊ እና የሲቪል ቁሳቁሶችን ሲያመርት የቆየ ሲሆን፤ አሁን ላይ በአዲስ መልክ ተደራጅቶ በአዲስ ስያሜ እና ተግባር በተወሰኑ ምርቶች በመገደብ ስራውን ይቀጥላል ተብሏል፡፡ 

ሜቴክ በአዲስ መልክ የሚደረግለት ለውጥ ‹‹የኮርፖሬሽን አደረጃጀት ማስተካከያ›› መሆኑን የሜቴክ የኮሜርሻልና ሲቪል ምርቶች ኦፕሬሽን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ አብዱልዓዚዝ መሀመድ ለሀገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል፡፡

‹‹ሜቴክ የብሔራዊ ኢንዱስትሪያል ምህንድስና ኮርፖሬሽን የሚል አዲስ ስያሜ ሊሰጠው ታስቧል፡፡›› ያሉት ኃላፊው፤ ድርጅቱ አዲሱን ስያሜ ይዞ የሲቪልና የንግድ ምርቶችን ብቻ እንደሚያመርት አክለዋል፡፡

የሜቴክ ወታደራዊ ምርቶችን የማምረት ስራ ለመከላከያ ሚኒስቴር እንደሚሰጥ ኃላፊው ገልጸዋል፡፡ ‹‹በሜቴክ ስር ወታደራዊ ምርቶችን ሲያመርቱ የነበሩ ኢንዱስትሪዎችን ለመከላከያ ሚኒስቴር በመስጠት ቀሪዎቹን በስሩ የሚያስቀጥል ይሆናል፡፡›› ብለዋል አቶ አብዱላዚዝ መሐመድ፡፡ 

ሜቴክን በአዲስ አደረጃጀት ለማዋቀር ሲባል አዲስ ረቂቅ ደንብ ተዘጋጅቶ በቅርቡ ለሚኒስትሮች ምክር ቤት እንደሚቀርብ የተገለጸ ሲሆን፤ ረቂቁ ከጸደቀ በኋላም ወደ ተግባር ይገባል ተብሏል፡፡

የብረታ ብረት እና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን-ሜቴክ በስሩ 14 ኢንዱስትሪዎች ያሉት ሲሆን፤ አራቱ ወታደራዊ ቁሳቁሶችን ሲያመርቱ ቆይተዋል፡፡ 

እንደ ተገለጸው ከሆነ፤ ሜቴክ በአዲሱ መዋቅራዊ ለውጥ መሰረት አራቱን ወታደራዊ ምርት ማምረቻ ኢንዱስትሪዎች ተነጥቆ ለመከላከያ ሚኒስቴር ለማስረከብ ይገደዳል፡፡

ቀሪዎቹ ዘጠኝ ኢንዱስትሪዎች ደግሞ በሜቴክ ወይም በአዲሱ ስያሜው ‹‹የብሔራዊ ኢንዱስትሪያል ምህንድስና ኮርፖሬሽን›› ስር እንደሚቀጥሉ ተነግሯል፡፡

ከዓመታት በፊት በአስር ቢሊዬን ብር የተቋቋመው ሜቴክ፤ በህወሓት ጄኔራሎች በሚመራበት ወቅት ለከፍተኛ የገንዘብ ብዝበዛ ተጋልጦ የቆየ ሲሆን፤ ዶ/ር ዐብይ አህመድ ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላ የአመራር እና መዋቅራዊ ለውጥ ተደርጓል፡፡ 

የስኳር ፋብሪካዎችን ጨምሮ ግዙፍ የመንግስት ፕሮጀክቶችን ያለ ምንም ጨረታ በመረከብ የሚታወቀው ሜቴክ፤ የተረከባቸውን ፕሮጀክቶች በጥራት እና በጊዜ ባለማስረከብ ‹‹ዝነኛ ስም›› አትርፏል፡፡ 

በበሊዬን የሚቆጠር የሀገር ሀብትም በዚሁ ድርጅት ለዓመታት ሲባክን እና ዚመዘበር እንደቆየ ከዚህ ቀደም በተደጋጋሚ ተነግሯል፡፡

No comments