Latest

ሸዋ፡- የጥንትና ዛሬ መገናኛ (ዲያቆን ዳንዔል ክብረት)

ሸዋ፡- የጥንትና ዛሬ መገናኛ  (ዲ. ዳንዔል ክብረት)

ዛሬ በተለምዶ ‹ሸዋ› እየተባለ የሚጠራውና ወደ ስድስት በሚጠጉ ዞኖች የተከፋፈለው የመሐል ኢትዮጵያ ክፍልን ታሪክ መረዳት የኢትዮጵያን ሕዝብ የውሕደት ታሪክ ለመረዳት ዓይነተኛ ማሳያ ነው፡፡ 


በሰሜን በዓባይ ወንዝና በበሽሎ፣ በመሐል ‹ሸዋ ሜዳ› እየተባለ በሚጠራው ሰፊ ሜዳ፣ በምሥራቅ በአዋሽ ወንዝ፣ በምዕራብ በወንጭት፣ በዠማና በሙገር ወንዞች፣ የተከበበ ነበር፡፡

ሴዋ (ሸዋ) የሚለውን ስም መጀመሪያ ለግዛታቸው የተጠቀሙት በይ(ኢ)ፋት አካባቢ ያለው ጥንታዊውን ግዛት የመሠረቱት ሙስሊም ሡልጣኖች ናቸው፡፡ ከ896/7-1285 በሸዋ ጠንካራ የሆነና እስከ ዘይላ ወደብ ድረስ ግዛቱንና ተጽዕኖውን ያስፋፋ የሙስሊም ሡልጣን ነበር፡፡ 

ኤንሪኮ ቼሩሊ እኤአ በ1936 በሐረር ከተማ አግኝቶ የቀዳው በ1863 የተጻፈው የዐረብኛ የእጅ ጽሑፍ ስለዚህ ጥንታዊ የሡልጣን ታሪክ የሚነግረን ብቸኛ ምንጫችን ነው፡፡ ይህንን ግዛት የመሠረተው ማሕዙሚ የተባለ ጎሳ ቤተሰብ ነበር፡፡ የዚህን ሡልጣናዊ ግዛት ድንበሮች በርግጠኝነት ለማመልከት አልተቻለም፡፡  

እንደ ቼሩሊ ያሉ ባለሞያዎች ግን በደቡብ ከጣርማ በር ተራሮች፣ አንሥቶ እስከ እንጦጦ ተራራ ይደርስ እንደነበር፣ በምዕራብ የሙገር ሸለቆ፣ በምሥራቅም ይፋትና ፈጠጋር ድረስ እንደተዘረጋ ገልጠዋል፡፡

የዚህ ሡልጣናዊ ግዛት ዋና ከተማው ‹ወለላሕ› ተብሎ ይጠራ ነበር፡፡ ቼሩሊ ይህንን ቦታ ከሸኖ በስተደቡብ፣ እንኮይ ወንዝ ሸለቆ ውስጥ የሚገኘው ‹ወለሌ› ነው ይላል፡፡ ይህንን የሡልጣን ግዛት በውስጡ ተነሥቶ የነበረ የሥልጣን ሽኩቻና በይፋት የተነሣው የወላዝማ ሥርወ መንግሥት አዳከሙት፡፡  

በመጨረሻም በ1275/76 የይፋት ሡልጣኖች ከተማዋን አጠፏት፡፡ የማሕዙሚ ሥርወ መንግሥትም በዚሁ ተጠናቀቀ፡፡ ምንም እንኳን በሸዋ ሡልጣን ግዛት ውስጥ የነበሩትን ሕዝቦች አጥርቶ የሚያሳይ ማስረጃ በበቂ ሁኔታ ባይገኝም፡፡ በሐረሩ መዝገብ ላይ ከሚገኙ የቦታና የሰዎች ስሞች ግን ፍንጭ ማግኘት ተችሏል፡፡ በግዛቱ ውስጥ ሴማውያን ሕዝቦች በብዛት እንደነበሩ ያሳያል፡፡

የሸዋ ሡልጣን ግዛት ዘመን ሲያልቅ ብቅ ያለው የይፋት ሥርወ መንግሥት ነው፡፡ ‹ይፋት› የሚለው ስም ‹አውፋት፣ ዋፋት› ከሚለው የዐረብኛ መጠሪያው ሳይመጣ አይቀርም፡፡ የግእዝ ጥንታዊ መዛግብት ‹ዊፋት› ብለው ይጠሩታል፡፡ 

በ1418 ዓም የተጻፈው ጥንታዊው ገድለ ተክለ ሃይማኖት በዚህ ስም ነው የሚጠራው፡፡ የይፋት ሥርወ መንግሥት መሥራቾች ወላዝማዎች ናቸው፡፡ እንደ ሸዋ ሡልጣኖች ሁሉ የዓረብ ዝርያ እንዳላቸው ይናገራሉ፡፡ ለብዙ ዘመናት የዳሞት ሥርወ መንግሥት ገባሮች የነበሩት ይፋቶች ራሳቸውን አጠናክረውና የሸዋ ሡልጣኖችን ድል አድርገው መንግሥታቸውን አደላደሉ፡፡  

ስለ ይፋት ሡልጣኖች አያሌ በዐረብኛ የተጻፉ መዛግብትን እናገኛለን፡፡ ኢብን ሰዒድ አል መግሪቢ፣ ኢብን ፋድላላ አል ኡማሪ፣ አል ማቅሪዚ፣ ኢብን ሐልደን፣ አል ቃልቃሻንዲ በዝርዝር ስለ ይፋት ይነግሩናል፡፡

ከ1277 እስከ 15ኛው መክዘ ሁለተኛው አጋማሽ ድረስ በመካከልና በደቡብ ኢትዮጵያ ከነበሩት ሰባት የሙስሊም ሡልጣኖች (ይፋት፣ ዓራባብኒ፣ ደራ፣ ደዋሮ፣ ሐድያ፣ ሻርሐ እና ባሊ(ባሌ)) መካከል ይፋት ገናናው ነበር፡፡ ከግድም ተነሥቶ የሰሜን ምሥራቅ ሸዋ ከፍታ ቦታዎች በመያዝ ከአዋሽ ማዶ እስካለው ሜዳ ይሻገራል፡፡  

በምሥራቅም እስከ ዘይላ ይደርስ ነበር፡፡ አል መቅሪዚ እንደሚነግረን የይፋት ግዛት ነዋሪዎች ቋንቋ ‹አቢሲንያዊ› ነበር፡፡ ይህም ቋንቋቸው የኢትዮ- ሴማዊ ቤተሰብ እንደነበረ ያመለክታል፡፡ ዋና ዋናዎቹ ነዋሪዎች አርጎባዎችና ዶብአዎች ነበሩ፡፡

በ13ኛው መክዘ የይኩኖ አምላክ መንግሥት በሸዋ ኃይሉን እያጠናከረ ሲመጣ የወላዝማ ሥርወ መንግሥት በውስጣዊ ሽኩቻ ውስጥ ተነክሮ ነበረ፡፡ ምንም እንኳን ከይኩኖ አምላክ ወራሾች ጠንካራ ዘመቻ ቢገጥማቸውም የወላዝማ ነገሥታት ግን ለብዙ ዘመናት መቋቋም ብቻ ሳይሆን አዳልንም ጨምረው እየገዙ ተጠናክረው ነበር፡፡

በኋላ ግን የውስጡ ሽኩቻና የክርስቲያኑ መንግሥት መጠናከር አቅማቸውን አዳከመው፡፡ ዐፄ ይስሐቅ በ1407 ታዋቂውን የይፋትን ሡልጣን ሳአ ዳዲን አቡ - ኢል በረከትን ከዘይላ ወደብ አጠግብ ድል አደረገው፡፡ ዐፄ ዘርአ ያዕቆብም የርሱን ሹሞች በይፋት ላይ ከመሾሙም በላይ ጨዋ የተባለውን ሠራዊት አሠፈረበት፡፡
Figure 1 ንጉሥ ይኩኖ አምላክ፣ ከሙስሊምና ክርስቲያን ሠራዊቱ ጋር
አሕመድ በድላይ የተባለው የወላዝማ ሥርወ መንግሥት ኃያል የጦር መሪ በ1428 ዓ.ም. ዋና ከተማውን ወደ ዳካር አዘዋወረ፡፡ ዋናውን የሀብት ምንጭና የንግድ መሥመርም አጣ፡፡ ነገር ግን ለተወሰኑ ዓመታት ሥርወ መንግሥቱን አጠናክሮ ለመቀመጥ ችሎ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ በተደጋጋሚ የሠነዘረው ጥቃት በለስ ቀናውና ዐፄ ዘርአ ያዕቆብ በ1437 አሕመድ በድላይን ድል አደረገው፡፡

እነዚህ ሁለቱ የሙስሊም ሡልጣኖች በምድረ ሸዋ በየዘመናቸው ሲገዙ ከደቡብ እየመጣ የሸዋን ደጋማ ቦታዎች የሚቆጣጠርና የሚያስገብር ሌላም ኃይል ነበር፡፡ መሠረቱን በዛሬዋ ወላይታ አካባቢ ያደረገው የዳሞት ሥርወ መንግሥት ከደቡበ ወደ መካከለኛው ኢትዮጵያ ተደጋጋሚ ወረራ አድርጓል፡፡ በኋላም ኃይሉን አጠናክሮ ከሸዋና ከይፋት ሥርወ መንግሥታት ጋር ተገዳድሮ ሸዋን ገዝቷል፡፡  

በገድለ ተክለ ሃይማኖት ላይ የምናገኘው ሞተለሚ የተባለው ንጉሥ ወደ ሸዋ ያደረገው የግዛት ማስፋፋት የዚህ አካል ነበር፡፡ ገድለ ቅዱስ ያሬድ በዛግዌ ሥርወ መንግሥት ጊዜ ሰርጸ ጴጥሮስ የተባለ ንጉሥ ወደ ሸዋ የዳሞትን ንጉሥ ለመውጋት ዘምቶ እንደነበር ይነግረናል፡፡ 

ነገር ግን ሰርጸ ጴጥሮስ አልተሳካለትም፡፡ ድል ሆነ፡፡ የዳሞትም ንጉሥ አንገቱን ቆርጦ የራስ ቅሉን የእህል መሥፈሪያ አደረገው፡፡ በ13ኛውና በ14ኛው መክዘ መግቢያ ግን በተወሰኑ የሸዋ ቦታዎች የዛግዌ መንግሥት ሹማምንት እንደነበሩ ገድለ አቡነ ቀውስጦስ ይተርክልናል፡፡

የዳሞት ሠርወ መንግሥት ከ10ኛው መክዘ ጀምሮ የዛሬውን ወለጋንና ምዕራብ ሸዋን ይዞ ከዓባይ በስተ ደቡብ የተዘረጋ ሰፊ የደቡብ ግዛት ነበር፡፡ በምዕራብ እስከ ዴዴሳ፣ በደቡብ እስከ ወላይታ ይደርሳል፡፡ ዋናዎቹ ነዋሪዎችም ክርስቲያን ያልሆኑ ሲዳማዎች ነበሩ፡፡ በንግሥታትና በነገሥታት ይመራ የነበረው ይህ የዳሞት ግዛት እንደ ባኑ - አል - ሐምውያ ያሉ ጠንካራ ሴት ንግሥታትን ያፈራ ግዛት ነበር፡፡ 

ይህቺ ንግሥት ከደቡብ ተነሥታ የአኩስምን ግዛት የተጋፋች፣ የአኩስምን ነገሥታት ከደቡብ ግዛታቸው እንዲያፈገፍጉ ያደረገች ኃያል ነበረች፡፡ በኋላም የራስዋን ነጻ ግዛት አቁማ ለብዙ ዘመናት የጸና ሥርወ መንግሥትን የመሠረተች ናት፡፡

የዳሞት ሥርወ መንግሥት ከ10 - 13ኛው መክዘ መጀመሪያ የአኩስምን በኋላም የዛግዌን ሥርወ መንግሥት ድል አድርጎ ጸንቶ ነበር፡፡ ከሰሜን የአኩስም መንግሥትን መዳከም ተከትሎ ወደ ደቡብ በመጡ ክርስቲያኖች እየተሠሩ የነበሩ አብያተ ክርስቲያናትን በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ዘመን መጥቶ በተደጋጋሚ ያጠፋው ይህ ገናና መንግሥት ነው፡፡ 

ከዚህ ገናና መንግሥት ጋር መጀመሪያ ተዋግቶ ያሸነፈው ይኩኖ አምላክ ነው፡፡ አረማዊ እምነትን ይከተል የነበረው የዳሞት መንግሥት በሸዋ ይኖሩ በነበሩ የክርስቲያንና የሙስሊም ማኅበረሰቦች ላይ ያደርስ የነበረው ተጽዕኖ ሁለቱን ማኅበረሰቦች እንዲተባበሩ አድርጓቸዋል፡፡ የይኩኖ አምላክ ወታደሮችም ከሁለቱም የተውጣጡ ነበሩ፡፡ ይበልጥ የዳሞትን መንግሥት ያስገበረው ግን ንጉሥ ዐምደ ጽዮን ነው፡፡

በ16ኛው መክዘ መጀመሪያ የዳሞት ግዛት ሰዎች ከፊል ክርስቲያንና ከፊል ሙስሊም ነበሩ፡፡ ክርስቲያን ዳሞቴዎች በአሕመድ ግራኝ ጦርነት ጊዜ ከአማራዎችና ትግራዮች ጋር በመሆን አሕመድ ግራኝን ተዋግተው ነበር፡፡ ከጦርነቱ ፍጻሜ በኋላ የሜጫ ኦሮሞዎች የዳሞትን ግዛት ተገዳደሩት፡፡ ብዙዎቹ ዳሞቴዎች ለሜጫ ኦሮሞዎች ገብረው ኦሮሞዎች ሆነው ሲቀሩ ከፊሎቹ በተለይ ክርስቲያን ዳሞቴዎች ግን የዓባይን ወንዝ ተሻግረው ወደ ጎጃም በመግባት ዛሬ በስማቸው በሚጠራውና ዳሞት በተሰኘው አካባቢ መኖር ቀጠሉ፡፡

በዚህ የዳሞት ግዛት ውስጥ ሌላም አንድ ገናና ሕዝብ ይኖር ነበር፡፡ የጋፋት ሕዝብ፡፡ እንደ ሕዝቡ ትውፊት ከሆነ ከአኩስም ዘመን ጀምሮ ወደ መካከለኛዋ ኢትዮጵያ ጋፋቶች ገብተዋል፡፡ ባሉን ጽሑፍ መረጃዎች ግን ጋፋቶችን በመካከለኛዋ ኢትዮጵያ የምናገኛቸው ከ13ኛው መክዘ ሁለተኛ አጋማሽ ጀምረን ነው፡፡  

እስከ አ16ኛው መክዘ ድረስ ጋፋቶች በዛሬው ምዕራብ ሸዋ(በተለይ ሙገር)፣ ምሥራቅ ሸዋ (ወንጂና ሞጆ አካባቢ)፣ መርሐ ቤቴ፣ ሰሜን ሸዋ (ጽላልሽ) ሰላሌ (ግራርያ) አካባቢ ይኖር የነበረ ሕዝብ ነው፡፡ ሕዝቡ ሰባት ቤት ጉዳም የተሰኘ ፌዴሬሽን ነበረው፡፡ ይህ ፌዴሬሽን የሰባት ቤት ጋፋት አንድነት ነው፡፡ እነዚህን የጋፋት ፌዴሬሽኖችን የተመለከተ መረጃ ኮንቲ ሮሲኒ ከኤርትራ አግኝቶ ወደ ጣልያንኛ ተርጉሞት ነበር፡፡

በዚህ መዝገብ መሠረት ሰባቱ የጋፋት ማኅበረሰቦች ወግዳ - መለዛይ፣ ድንቢ- ደበራይ፣ ሙገር - እንደዛቢ፣ ወጅ - እነጋሪ፣ ወረብ - እነካፌ፣ ጽላልሽ - እነጋፊ፣ መዋል - እወዣዣይ ናቸው፡፡ እነዚህ ማኅበረሰቦች በብረታ ብረት ቴክኖሎጂያቸው የታወቁ ናቸው፡፡ የዚያ ኢንዱስትሪያቸው ቅሬት ዛሬም ሙገር ሸለቆ ውስጥ ከአቡነ ተክለ ሐዋርያት ገዳም ማዶ በሚገኘው ዋሻ ውስጥ ይታያል፡፡  

የእነዚህ ሰባቱ ጋፋቶች አለቃ መለዛይ ከንጉሥ ይኩኖ አምላክ ጋር ቃል ኪዳን ገብቶ ተባብሮ ነበር፡፡ እነዚህን የሚመራው አለቃ ‹የጉደም አለቃ› ተብሎ እንደሚጠራ ገድለ አቡነ አኖሬዎስ ይነግረናል፡፡ በአቡነ አኖሬዎስ ዘመን የነበረው የጉደም አለቃ ‹ሳፋይ› ይባል ነበር፡፡ እነዚህ ሕዝቦች ዛሬ ተውጠውም ተሰደውም ቢጠፉም ሙገር፣ ወጅ፣ ወግዳ፣ ጽላልሽ፣ ግንደ በረት፣ ግራርያ የተሰኙት አካባቢዎቻቸው ግን ስማቸውን ለታሪክ አቆይተውላቸዋል፡፡

ስለ ጋፋቶች ወደ ኢትዮጵያ የገቡ አውሮፓውያን (አልቫሬዝ፣ ቤርሙዴዝና አልሜዳ) ጽፈውላቸዋል፡፡ እነዚህ ጸሐፍት እንደሚነግሩን በ16ኛው መክዘ ጋፋቶች በዓባይ ሸለቆ ምዕራባዊ ዳርቻ ከወለቃ(ደቡብ ወሎ) አንሥቶ እስከ ወለጋ ዴዴሳ ወንዝ ድረስ በዳሞት ግዛት ይኖሩ ነበር፡፡ በደቡብም እስከ አዋሽ መነሻ ድረስ ይደርሳሉ፡፡  

ይህ ዛሬ ምዕራብ ሸዋ በተባለው አካባቢ የነበረው ግዛታቸው ምንም በዳሞት ሥር ቢሆን የቦታው ስያሜ ግን ወረብ የተሰኘ በአንደኛው የፌዴሬሽኑ አባል የተሰየመ ነበር፡፡ ከአሥራ ሁለቱ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ደቀ መዛሙርት አንዱ አቡነ አኖሬዎስ የተሸመው ለወረብ ነበር፡፡ ዛሬ ይህ ቦታ ስሙ ተቀይሮ በሜታ አቦ የምትገኘው የቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ብቻ ደብረ ወረብ ቅድስት ማርያም ተብላ ወርሳው ቀርታለች፡፡ 

ልክ የናዝሬት ስም ወደ አዳማ ሲቀየር የናዝሬት ቅድስት ማርያም ደብረ ናዝሬት ቅድስት ማርያም ሆና ታሪክ እንደወረሰችው፡፡ የወረብ ሰዎች በ17ኛው መክዘ ወደ ጎጃም መጥተው በዓባይ ወንዝ አጠገብ ኖረዋል፡፡ ዛሬም በዓባይ ወንዝ ሰሜን፣ በባሕር ዳር አጠገብ ወረብ የምትባል መንደር አለች፡፡

ከ14ኛው መክዘ በኋላ ጋፋቶች አንዳንድ ጊዜ ከማዕከላዊው መንግሥት ጋር ሲተባበሩ፤ ሌላ ጊዜ ሲያምጹ ኖረዋል፡፡ በ15ኛው መክዘ ጋፋቶች በከፊል ክርስትናን እየተቀበሉ መጥተዋል፡፡ ገድለ እጨጌ ዕንባቆም በ15ኛው መክዘ የነበረውን የጋፋቶች ሕይወት በሚገባ ያሳየናል፡፡ በአሕመድ ኢብራሂም ጊዜ ደግሞ እስልምናን የተቀበሉ ጋፋቶች ነበሩ፡፡ በዐፄ ሰርጸ ድንግልና በዐፄ ሱስንዮስ ዜና መዋዕሎች ጋፋቶችን እናገኛቸዋለን፡፡

በ16ኛው መክዘ መጨረሻ ጋፋቶች በአካባቢው ኃይል እያገኙ የመጡትን የኦሮሞ ማኅበረሰቦች መቋቋም አልቻሉም፡፡ የዓባይን ወንዝ እንደ ተፈጥሯዊ መከላከያ ስላዩት ዓባይን እየተሻገሩ ወደ ጎጃም ገቡ፡፡ በርግጥ ገድለ አቡነ ተክለ ሐዋርያትንና ገድለ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን ስንመለከት ጋፋቶች ከ13ኛው መክዘ አስቀድመው ወደ ጎጃም ተሻግረው ነበር፡፡ በዚያም ጠንካራ ማኅበረሰብ ነበራቸው፡፡ በሸዋና በወለጋ የነበሩት ጋፋቶች ወደ ጎጃም እንዲሻገሩ ያደረጋቸው ቀድመው ዘመዶቻቸው ስለተሻገሩ ይሆናል፡፡

ታሪክ በሸዋ እንዲህ ስትፈስ ሌሎችም ሕዝቦች ከሰሜን ወደ ሸዋ ከ8ኛው መክዘ ጀምረው ይገቡ ነበር፡፡ ከትግራይ ወደ አምሐራ ከአምሐራም ወደ ሸዋ የገቡ የትግራይ ማኅበረሰቦች ነበሩ፡፡ ገድለ ተክለ ሃይማኖት ይህን ፍልሰት በዝርዝር ይተርክልናል፡፡ ከዋድላ ወደ ሸዋ የሚደረግ የቤተ አምሐራ ፍልሰትም ነበር፡፡ ከዚያ ቀደም ብሎ በሸዋ አካባቢ የቤተ አምሐራና ትግራይ ሰዎች ካልኖሩ በቀር በመዛግብት በተመዘገበው መጠን ፍልሰት ሊኖር አይችልም፡፡ 


በ10ኛው መክዘ አካባቢ የአኩስም ጽዮንን የያዙ የአኩስም ካህናት ወደ ሸዋ መጥተው የመከራውን ጊዜ በዝዋይ ደሴት አሳልፈዋል፡፡ እነዚህ ካህናት ዝም ብለው ወደ ደቡብ አይመጡም፡፡ ከዚያ በፊት ለብዙ መቶ ዓመታት ያህል ከሰሜን ወደ ደቡብ ፍልሰት ነበር ማለት ነው፡፡ የአኩስም መንግሥትን መዳከም ተከትሎ ብዙ ማኅረሰቦች ወደ ሸዋ መጥተዋል፡፡ ይህ ተከታታይ ፍልሰት ያቆየው የጉዞ ታሪክ ነው የአኩስምን ካህናት ወደ ደቡብ የሳባቸው፡፡ የዛይ ማኅበረሰብ ታሪክም ይህንን የሚያስረግጥ ነው፡፡

በአኩስም መንግሥት ፍጻሜ የሰሜን ሕዝቦች ወደ ደቡብ ዝም ብለው አልመጡም፡፡ ቀደም ብሎ ከክርስትና መስፋፋት ጋር በተያያዘ ወደ ደቡብ የመጡ ሰሜናውያን ፈላሲዎች ነበሩ፡፡ እነርሱም እስከ ዛሬ ድረስ ጸንተው የቆዩ የታሪክ ማስረጃዎችን ትተውልናል፡፡ በየካ ተራራ ላይ የሚገኘው ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን፣ የአዳዲ ማርያም ውቅር ቤተ ክርስቲያን፣ በጋሞ የምትገኘው የብርብር ማርያም፣ የዔሊ ገብርኤል አብያተ ክርስቲያናት፣ በየረር ተራራ ላይ ዛሬም ፍራሻቸው የሚገኘው አብያተ መንግሥትና አብያተ ክርስቲያናት፤ በሞረት የሚገኘው የደይ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ምስክሮች ናቸው፡፡  


በወላይታ ሥርወ መንግሥት ውስጥ ‹ትግሬ› የተሰኘ ሥርወ መንግሥት መኖሩ የዚህ ግንኙነት ውጤት ነው፡፡ በእንጦጦ(ስለዚህ ቦታ ገድለ አባ ኤልያስ ዘእንጦጦ በዝርዝር ይተርካል፤ የዐፄ ምኒልክ ታሪከ ነገሥትም የእንጦጦ ራጉኤልና ኪዳነ ምሕረት ሲሠሩ ስለ ተገኙ ፍራሾች ይነግረናል)፣ በጅባትና በእንስላል(ከየረር ተራራ በስተ ምዕራብ፣ እንስላል ጢቆ) የሚገኙ ቅሬቶች ሕያዋን ሆነው ዛሬም ይናገራሉ፡፡ ከየረር ተራራ በስተ ምሥራብ፣ ከሲሬ 6 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የተገኘው የጊምቢ ጥንታዊ ቤተ ክርስቲያን ፍራሽም ሌላው ማሳያ ነው፡፡ የአሕመድ ኢብራሂም ታሪክ ጸሐፊ እንደሚነግረንም በዝቋላ ሥር ላሊበላ የሚባል ከተማ ነበረ፡፡  

በቅርቡ ገርጂ(አዲስ አበባ) በቁፋሮ የተገኘው የመካከለኛው ዘመን ቤተ ክርስቲያን ከእነዚህ ጥንታውያን ቅርሶች አንዱ ነው፡፡ አራት ማዕዘን በነበረው በዚህ ጥንታዊ ቤተ ክርስቲያን ቦታ ላይ ነው የረር ሥላሴ የተሠራው፡፡(ANFRAY Francis, 1978, «Enselale, avec d’autres sites du Choa, de l’Arsi et un îlot du Lac Tana », Annales d’Éthiopie, vol. XI, p. 153-169.) ከ13ኛው እስከ 16ኛው መክዘ በንግድ መሥምር ተርታ የተሠሩ ንጉሣውያን አድባራት ነበሩ (እንስላል - ጊንቢ - ጎጂ ኪዳነ ምሕረት - ጎቶ - ኢላላ ገዳ - ኢጀርሳ)፡፡


መጀመሪያ አናሳ ማኅበረሰብ የነበሩት ከቤተ አምሐራና ከትግራይ የመጡት ክርስቲያኖች በኋላ ግን የይኩኖ አምላክን ወደ ሸዋ መምጣት ተከትሎ ጠንካራ ማኅበረሰቦች ሆኑ፡፡ በሸዋ ከነበሩት ሌሎች ማኅበረሰቦች ጋር በመሆንም ማዕከላዊውን መንግሥት አጠናከሩ፡፡ ሦስቱ የንግድ መሥመሮችንም እነዚህ የሸዋ ማኅበረሰቦች እንደ ወቅታዊ ዐቅማቸው እየተፈራረቁ ይይዟቸው ነበር፡፡ ወደ ምሥራቅ ወደ ዘይላና በርበራ የሚሄደው፣ በመርሐ ቤቴ ተሻግሮ በወለቃ በኩል ወደ ሰሜን የሚጓዘውና አዋሽን ተሻግሮ ወደ ደቡብ የሚያመራው፡፡

ከትግራይና ከቤተ አምሐራ የመጡት በብዛት ክርስቲያን የነበሩት ሕዝቦች ማዕከላዊውን መንግሥት በመጠቀም በዋናነት የእርሻ መሬቶችን፣የንግድ መሥመሮችንና አካባቢያዊ ሥልጣኖችን ያዙ፡፡ ከዚያ በፊት ዳሞቶችና ጋፋቶች ይዘዋቸው የነበሩ ሥልጣኖችና የኢኮኖሚ ቦታዎች በእነርሱ ቁጥጥር ሥር ዋሉ፡፡ ከዋነኞቹ የሸዋ አንቀሳቃሽ ኃይሎችም ጋር ተሰለፉ፡፡ እስከ 16ኛው መክዘ የደጋው ነዋሪዎች የእርሻ ቦታዎች በጋፋቶች፣ ዳሞቶች፣ አምሐራዎች፣ ኦሮሞዎችና ትግራዮች የተያዘ ነበር፡፡ 


በተለይም ክርስቲያኖቹ አያሌ አብያተ ክርስቲያናትንና ገዳማትን መካከለኛዋ ኢትዮጵያ ተክለዋል፡፡ በመካከለኛው ዘመን መጨረሻ በግድም (ከቤተ አምሐራ ደቡብና ከመንዝና ግሼ በስተ ምሥራቅ) እርስ በርሳቸው የተዛመዱ ክርስቲያንና ሙስሊም አምሐራዎች በደጋው፣ ክርስቲያንና ሙስሊም አፋሮችም በቆላው ይኖሩ እንደነበሩ ፕሮፌሰር መርእድ Southern Ethiopia and the Chrstian Kingdom 1508-1708, With special reference to the Oromo migrations and their consequences በተሰኘው ጥናታቸው ላይ ይገልጣሉ፡፡

ሸዋ ውስጥ የነበሩ ልዩ ልዩ ሕዝቦች ተባብረው ማሶንን (ሞጆ ወንዝ አጠገብ የነበረ ከተማ፡፡ በነገራችን ላይ ሞጆ የሚለው ቃል ከ16ኛው መክዘ በፊትም ጥቅም ላይ የዋለ ስም እንደ ነበር ፉቱሕ አል ሐበሻ ይነግረናል)፣ በረራንና ባዶቄን የመሰሉ ታላላቅ ከተሞችም ተቆርቁረዋል፡፡ እነዚህ ከተሞች በመካከለኛዋ ኢትዮጵያ የነበሩ ሕዝቦች የጋራ መናኸሪያ ከመሆን አልፈው ከውጭ የመጡት ቬነሳውያን፣ ፖርቹጋሎች፣ ጣልያናውያንና ግብጾችም ይኖሩባቸው ነበር፡፡ በ16ኛው መክዘ መጀመሪያ የኦሮሞ ሕዝብ በሚጠናከር ጊዜ እነዚህ ማኅበረሰቦች ጫናውን መቋቋም አቃታቸው፡፡ የሮበሌ - ገዳ ለመጀመሪያ ጊዜ በ1565 ዓም ወደነዚህ ሕዝቦች መስፋፋት ጀመረ፡፡ 


በዐፄ ሰርጸ ድንግል ዘመነ መንግሥት መጨረሻም ጫናውን መቋቋም ያቃታቸው ሸዋን ለቅቀው ወደ ጎጃም ተሻገሩ፡፡ ሌሎቹ ተዋጡ፤ እንቋቋማለን ያሉት ደግሞ ደጋ ደጋውን ትተው ተፈጥሯዊ መከላከያ ፍለጋ ወደ ቆላው ወረዱ፡፡ የሸዋ ማኅበራዊ የኑሮ መልክዐ ምድርም(demography) ለመጨረሻ ጊዜ(de facto) ተቀየረ፡፡ በ16ኛው መክዘ መጀመሪያ የሸዋ አብዛኛው ክፍል በኦሮሞዎች ተያዘ፡፡ የሸዋን ምዕራባዊ ክፍልና ወለቃንም የቦረና ጎሳዎች ያዙት፡፡ቱለማ መካከለኛውን የሸዋ ክፍል ሲይዝ፣ ከረዩም ምሥራቃዊውን ሸዋ ያዘ፡፡  

ወደ ወሎም ተሻገረ፡፡ ዛሬ በሸዋ የሚገኙት አማሮችና ኦሮሞዎች ሁለቱም ንጥል ጎሳዎች አይደሉም፡፡ እርስ በርሳቸውና ከሌሎች ዛሬ ከታሪካቸው በቀር ሕልውናቸውን ከማናገኘው ሌሎች ሕዝቦች ጋር የተዋሐዱ ናቸው፡፡ ለሸዋ ኦሮሞዎች ከሸዋ አማሮች፣ ለሸዋ አማሮችም ከሸዋ ኦሮሞዎች በላይ የሚዛመዳቸውና የሚቀርባቸው የለም፡፡ ሁለቱም እርስ በርስ ተዛምደዋል፤ ሁለቱም ከተመሳሳይ ሌሎች ሕዝቦችም ጋር ተዛምደዋል፡፡

ኦሮሞዎች በብዛት በሸዋ ከመስፋፋታቸው በፊት ከሌሎች ማኅበረሰቦች ጋር በዚህ በሸዋ ምድር ይኖሩ ነበር፡፡ ምንም እንኳን ዋናው ማዕከላቸው በደቡብ ኢትዮጵያ ከስምጥ ሸለቆ ግራና ቀኝ ቢሆንም ቀደም ብለው (ከመካከለኛው ዘመን ቀደም ብለው) በመካከለኛው ኢትዮጵያ የሚኖሩ የኦሮሞ ማኅበረሰቦች በተለይ በሸዋ ልዩ ልዩ ክፍሎች እንደነበሩ ገድለ አቡነ ቀውስጦስ የሚሰጠን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ በዐፄ ዳዊት ዘመን(1374-1406 ዓ.ም) የተጻፈው ይህ ገድል ብዙ ጥንታውያን ቅጅዎች አሉት፡፡ የምጠቅሰው በ2007 ዓ.ም. የኢቲሳ ተክለ ሃይማኖት ገዳም ያሳተመውን ቅጅ ነው፡፡ ለተደራሽነቱ ሲባል፡፡

ገድሉ በአንድ ቦታ ላይ ‹ዘሀለወት ደብር ወበል ስማ ሰገሌ - ሰገሌ የምትባል ደብር ነበረች› ይላል፡፡ በሌላም ቦታ ‹ደብረ ሰገሌ› ይላታል (Gli Atta di Qawsetos, 240) ሰገሌ ኦሮምኛ ነው፡፡ ‹ድምጽ› ማለት ነው፡፡ ‹ግበር ሎቱ(ለገላውዴዎስ) መልዕልተ የይ፤ ወለቴዎድሮስ ላዕለ ደብረ መንዲዳ - ለገላውዴዎስ በየይ ተራራ ላይ (ቤተ መቅደስ) ሥራ፤ ለቴዎድሮስ ደግሞ በመንዲዳ ተራራ ላይ› ይላል(ገጽ 119፤139)፤ መንዲዳ ኦሮምኛ ነው፡፡ ‹የዱር ቤት› እንደማለት ነው፡፡ ዛሬ ከደብረ ብርሃን ከተማ ወደ የጁ በሚወስደው መንገድ መንዲዳ የምትባል ከተማ አለች፡፡ ‹ወለፊቅጦርኒ በሀገረ ለሚ ዘትሰመይ ደብረ ዲባናው - ፊቅጦርንም ደብረ ዲባናው በምትባል በለሚ ሀገር› ‹ለሚ›፣ በኦሮምኛ ‹ዜጋ› ማለት ነው፡፡ 


‹ወይብሉ ርእዩ ሰብአ ገላን ወየይ - የገላንና የየይ ሰዎችን ተመልከቱ አሉ›(ገጽ 121)፤ ገላን የኦሮሞ ጎሳ ስም ነው፡፡ ‹ወአጥመቆሙ በህየ ሰብአ የይ፣ ወመሐግል ወገላን፣ ወሰብአ ጋሞ ወወላሶ ወቀጨማ - የየይን፣ የመሐግልንና የገላንን፣ የጋሞን፣ የወላሶ(ወሊሶ)ና የቀጨማን ሰዎች አጠመቃቸው›(ገጽ 137)፡፡ ወላሶ(ወሊሶ) ዛሬ በስሙ ከተማ የተሠራለት የኦሮሞ ማኅበረሰብ ስም ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች በሸዋ ከወግዳ አጠገብ የነበሩ ናቸው፡፡ መሐግል በዛሬው ቡልጋ አካባቢ ይገኝ የነበረ ነው፡፡ ጋሞዎች በኋላ ዘመን ወደ ደቡብ ከመገፋታቸው በፊት በመካከለኛው የኢትዮጵያ ክፍል የነበራቸውም ቦታ ያሳየናል፡፡

‹ወአጥመቆሙ ለሰብአ ይእቲ ሀገር ውስተ ፈለገ ጨንጌ - የዚያችን ሀገር ሰዎች በጨንጌ ወንዝ አጠመቃቸው› ይላል(ገጽ 139)፡፡ ጨንጌ ኦሮምኛ ነው፡፡ ዛሬ በአርሲ ዞን ሁሩታና ሲሬ ወረዳዎች መካከል የሚገኝ ጨንጌ የሚባል ሥፍራ አለ፡፡ እንደ ገድሉ ከሆነ ወንዙ ከመሐግል (ዛሬ ቡልጋ አካባቢ) ብዙም አይርቅም፡፡ ምናልባት በዚህ አካባቢ የነበሩ የኦሮምኛ ተናጋሪዎች በኋላ ወደ አርሲ ሄደዋል ወይም ተመሳሳይ ሌሎች ማኅበረሰቦች በአርሲ ሰፍረዋል፡፡ አቡነ ቀውስጦስ የሰማዕቱ የቴዎድሮስ ቤተ ክርስቲያን በተሠራበት በመንዲዳ (በዚህ ስም የሚጠራ ቦታ በደብረ ብርሃንና በእነዋሪ መካከል አለ) ሄደው ‹ወአጥመቆሙ ለሕዝባ ውስተ ሰኮሩ - ሕዝቦቿንም በሰኮሩ ወንዝ አጠመቃቸው› ይላል(ገጽ 139)፡፡ ሰኮሩ ኦሮምኛ ነው፡፡ ‹እሾማ ቁጥቋጦ› እንደ ማለት ነው፡፡ በዚህ ስም የሚጠሩ ቦታዎች በጅማና በአርሲ አሉ፡፡

ከሰርማት እስከ ንብጌ ያሉ ሰዎችን በጥንቆላ ስለምታስት ሴት ሲተርክ ‹ወሰብአ ጎርፎኒ ወቅዱስጌ ይሰግዱ ላቲ - የጎርፎና የቅዱስጌ ሰዎች ይሰግዱላታል› (ገጽ 139) ይላል፡፡ ሰርማት ከመሐግል አጠገብ የነበረ ቦታ ነው፡፡ ከቡልጋ ብዙም የማይርቅ፡፡ በዚህ አካባቢ ጎርፎ የሚባሉ ማኅበረሰቦች ይኖሩ ነበር፡፡ ጎርፎ ዛሬ በምዕራብ ሸዋ በቾ ወረዳ የሚኖር የኦሮሞ ጎሳ ስም ነው፡፡ አብረዋቸው የተጠቀሱት የ‹ቅዱስጌ› ሰዎች ናቸው፡፡ ስያሜው ሴማዊ ነው፡፡ ‹ጌ› የአቅጣጫ አመልካች ነው፡፡ ሴማውያንና ኩሻውያን በሸዋ በጉርብትና ይኖሩ፣ በእመነትም ይተባበሩ እንደነበር ማሳያ ነው፡፡

አቡነ ቀውስጦስ የሰርማትን ወንዝ ተሻግሮ ጠንቋይዋን አገኛት፡፡ ‹ወውእቱኒ ተንሥአ ወሖረ መንገለ ሀገራ ለመሠሪት ዘስማ ሠሪቲ፡፡ ወአደወ ፈለገ ሰርማት ወረከባ በጽንፈ ማይ - እርሱም ተነሣና ሠሪቲ የተባለችው ጠንቋይ ወደዳለችበት ወደ ሀገሯ አቅጣጫ ሄደ፡፡ የሰርማትንም ወንዝ ተሻግሮ በባሕሩ ዳር አገኛት› ይላል(ገጽ 140)፡፡ ‹ሠሪቲ› ኦሮምኛ ነው፡፡ ‹ውሻ› ማለት ነው፡፡ በተለይም አንቋሽሾ ለመጥራት የሚውል ነው፡፡ ሴትዮዋ በጥንቆላዋ ምክንያት የወጣላት የማንቋሸሽ ስም ነው፡፡

ገድሉን በሚገባ ብናጠናው ብዙ እናገኛለን፡፡ ለዛሬ እዚህ ላይ ይብቃን፡፡ የኦሮሞ ሕዝብ በመካከለኛዋ ኢትዮጵያ ከሌሎች ሕዝቦች ጋር በአንድነት ይኖር የነበረ ሕዝብ ነው፡፡ በኋላ በ16/17ኛው መክዘ ኃይል አግኝቶ ሌሎችን አስገበረ እንጂ ለአካባቢው አዲስ ሕዝብ አይደለም፡፡ ተነጥሎ ኖሮም አያውቅም፡፡ የመገበርና የማስገበር ባሕሉም እንደሌሎቹ የኢትዮጵያ ማኅበረሰቦች ተመሳሳይ ነው፡፡

ገድለ ኢየሱስ ሞአ እንደሚለውም የይኩኖ አምላክ እናት የሰገራት መኮንን የነበሩት የአዛዥ ጫላ አገልጋይ ነበረች፡፡ ይህም ኦሮሞዎች በማዕከላዊው መንግሥት የነበራቸውን ቦታ የሚያሳይ ነው፡፡ ከ1680 ዓም በፊት በአምሐራ ሳይንት ኦሮሞዎች ከአምሐራዎች ጋር በሰላም ይኖሩ እንደነበር ደብረ ሊባኖስ እንዴት እንደቀናች በሚገልጠውና ከገድለ ተክለ ሃይማኖት ጋር ተጽፎ በተገኘው መዝገብ ላይ ፍንጭ እናገኛለን፡፡ 


በዚህ መዝገብ ላይ ደብረ ሊባኖስን በ1680 ዓም አካባቢ ከአምሐራ ሳይንት መጥተው ከጎበኟትና ሊያቀኗት ከተነሡት አራት ወንድማማቾች አንዱ ‹ጨፌ› የተባለ ሰው መሆኑን ይነግረናል፡፡ ጨፌ ኦሮምኛ ነው፡፡ የሦስት ወንድሞቹ ስሞች ገዴ፣ ሊቄና ዳኛ መባሉን ስናይ ዘመናትን የፈጀ ማኅበራዊ መስተጋብር ካልተፈጠረ በቀር በአንድ ቤተሰብ ውስጥ የሁለት ቋንቋ ስሞች እንደማይፈጠሩ አመላካች ነው፡፡ ዛሬ በዚህ ዘመን ከታሪካዊው እውነታው ርቀን እንደምናወራው ሳይሆን በኦሮምኛና በአማርኛ ስሞች የሚጠሩ ወንድማማቾች በአንድ ቤተሰብ ውስጥ ነበሩ፡፡

በዚህ የመካከለኛው ኢትዮጵያ የሕዝቦች መስተጋብር ውስጥ ጉራጌዎችን፣ አርጎባዎችንና ሐድያዎችን መዘንጋት አይቻልም፡፡ ጉራጌዎች ጥንት የነበሩበት ቦታ ከዛሬው የሰፋ ነበር፡፡ በምዕራብ ከጊቤ(ኦሞ) ወንዝ፣ በሰሜን ምዕራብ የዋቢ ወንዝ፣ በሰሜንም የአዋሽ ወንዝ ነበር ዳርቻቸው፡፡ በአካባቢያቸው ከነበሩ የኦሮሞ፣ የሲዳማ፣ የሐድያና የከምባታ ሕዝቦች ጋር ማኅበራዊ መስተጋብራቸው ላቅ ያለ ነበር፡፡  


በጉራጌ ሕዝብ ዘንድ ለረጅም ዘመናት የኖረውና የታወቀው የቃል ታሪክ የጉራጌን ሕዝብ መነሻ ከሰሜን ኢትዮጵያ ከትግራይ ያደርገዋል፡፡ በአዝማች ስብሐት ከጉርዐ የመጣው ሕዝብ በመካከለኛው ኢትዮጵያ ሠፍሮ መስፋፋቱን ይገልጣል፡፡ ነገር ግን የቋንቋ ጥናቶችን ስንመለከት የጉራጌ ሁሉም ዘየዎችና ማኅበረሰቦች የሚገኙት በመካከለኛዋ ኢትዮጵያ በመሆኑ ከሰሜን ወደ ደቡብ መጡ የሚለውን በምንጭነት ለመቀበል ከባድ ነው፡፡ በሰሜን ቅሬቱ የለምና፡፡ ሌላው ትርክት ደግሞ ከምሥራቅ ኢትዮጵያ ወደ መካከል እንደመጡ የሚተርክ የቃል ታሪክም አለ፡፡ በተለይም በስልጤ፣ በወለኔ፣ በገደባኖና በዛይ ዘንድ ይተረካል፡፡

ያም ሆነ ይህ ግን የጉራጌ ሕዝብ ከሰሜንና ከምሥራቅ የመጡ የሴም ቋንቋ ተናጋሪዎችንና በመካከለኛዋ ኢትዮጵያ የነበሩ የኩሽ ቋንቋ ተናጋሪዎችን ያዋሐደ ጥንታዊ የመካከለኛዋ ኢትዮጵያ ሕዝብ ነው፡፡ በዳሞትና በወረብ፣ በቢዛሞና በሌሎች የመካከለኛው ዘመን ግዛቶች ውስጥ በልዩ ልዩ መንገድ ይኖር የነበረው የጉራጌ ሕዝብ አሁን ያለበትን ቦታ የያዘው የአሕመድ ግራኝን ጦርነትና የኦሮሞ ሕዝብ መስፋፋትን ተከትሎ ነው፡፡

ከሰሜን ትግራይ በወሎ በኩል ወደ ሸዋ ዘልቆ እስከ ሐረርጌና ባሌ የተዘረጋው የአርጎባ ማኅበረሰብ መካከለኛዋን ኢትዮጵያ ካቀኑ ጥንታዊ ሕዝቦች መካከል ነው፡፡ የዛሬዎቹ አርጎባዎች በይፋት ሥርወ መንግሥት መሥራችነትና ገዥነት ትልቅ ቦታ ነበራቸው፡፡ ሰሜን ምሥራቅ ሸዋም የግዛታቸው ማዕከል ነበር፡፡ በአሕመድ ኢብራሂም ጦርነትና በኦሮሞ መስፋፋት ምክንያት አርጎባዎች ዋናውን ቦታቸውን እየለቀቁ ከሰሜን እስከ ደቡብ ተበታትነዋል፡፡ በሰሜን ከአምሐራ፣ በደቡብና በምሥራቅ ደግሞ ከኦሮሞዎች ጋር እየተዋሐዱ ቁጥራቸው ቢቀንስም ለዘር ግን ዛሬም አሉ፡፡

ሐድያዎች በኢትዮጵያ መዛግብት ውስጥ ስማቸው ቀድሞ ከሠፈሩ ማኅበረሰቦች ወገን ናቸው፡፡ ክብረ ነገሥት ሐድያ የተባለ የሙስሊም ግዛት እንደነበር በመናገር ቀዳሚው ነው፡፡ ከ9ኛው መክዘ ጀምሮ በሸዋ ታላቅ ቦታ እንደነበራቸው የሚያሳዩ መዝግብት አሉን፡፡ የዐፄ ዓምደ ጽዮን ዜና መዋዕልም በ1324/5 ወደ ይፋት ባደረገው ዘመቻ ‹አማኖ› ከተባለው የሐድያ መሪ ጋር ተዋግቶ ነበር፡፡ በዚህ ጦርነት አማኖ ተሸንፎ ወደ ይፋት ሸሸ፡፡ 


ከሦስት ዓመት በኋላም ሐድያ ዐምጾ ነበር፡፡ በኋለኞቹ መዛግብት ሐድያን የመካከለኛው መንግሥት አካል ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ሐድያዎችም በንጉሣውያን ሥፍራዎች ውስጥ ገብተዋል፡፡ በዐፄ ይስሐቅም ሆነ በዐፄ ዘርአ ያዕቆብ ዘመን ሐድያዎች የራሳቸውን ነጻ ግዛት ለማስጠበቅ በተደጋጋሚ ዐምጸው ነበር፡፡ ግን አልተሳካም፡፡

ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ የሐድያው ገዥ የገራድ መሐመድን ልጅ ዕሌኒ መሐመድን በ1436 ዓም አግብቶ ነበር፡፡ ዕሌኒ ምንም እንኳን ልጅ ባይኖራት በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ታላቅ ቦታ የነበራት ሴት ነበረች፡፡ በዐፄ ዘርአ ያዕቆብ፣ በዐፄ በዕደ ማርያም፣ በዐፄ እስክንድር፣ በዐፄ ናዖድና በዐፄ ልብነ ድንግል ዘመን ኖራለች፡፡ ይህንን ዘመን ታሪክ ጸሐፊው ‹የኢትዮጵያ ታላላቆች እንደ ባሕር ዐሣ እርስ በርሳቸው ተዋዋጡ፤ መኖሪያ እንደሌላቸው አራዊትም ሆኑ› ይለዋል፡፡ ከፍተኛ የሥልጣን ሽኩቻ የነበረበት ዘመን በመሆኑ፡፡

ዕሌኒ ከሽቻው ውጭ ሆና በመንፈሳዊ ሕይወት ላይ በማተኮሯ ሕዝቡ ወደዳት፤ እንደ ሀገር ዋርካም ቆጠራት፡፡ በዚያ ዘመን 1500 ዓም ሲገባ ስምንተኛው ሺ ገባ ተብሎ ታምኖ ነበር፡፤ ሕዝቡም ሀገራዊውን መደበላለቅ ከዚህ ጋር አያያዘው፡፡ በዚህ ዘመን የተረጋጋና መንፈሳዊ እሴት ያላው ታላቅ ሰው ይፈለግ ነበር፡፡ እሌኒ ዘመኑ የሚፈልገው ዓይነት ሰብእና ነበራት፡፡ 


ንጉሥ ልብነ ድንግል ነሐሴ 8 ቀን 1500 በልጅነቱ ሲነግሥ የዙፋን ጠባቂዋ ዕሌኒ ነበረች፡፡ በወቅቱ በኢትዮጵያ ለነበረው ለፍራንሲስኮ አልቫሬዝ አቡነ ማርቆስ እንደነገሩት ‹እርሳቸውና ንግሥት ዕሌኒ ልብነ ድንግልን አነገሡት፤ ምክንያቱም ሁሉም የኢትዮጵያ ታላላቆች በእነርሱ እጅ ነበሩና፡፡› አልቫሬዝ እንደሚለው የሀድያ ተወላጇ ንግሥት ዕሌኒ በጎጃም ሰፊ ርስት ነበራት፡፡ ከዙፋኑ ሽኩቻ ወጣ ብላ በመኖሯ በሀገሪቱ እየመጣ ያለው የሙስሊም ክርስቲያን የእርስ በርስ ጦርነት ቀድማ ለማየት በቅታ ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት ማቴዎስ የተባለውን አርመናዊ ለጦር ርዳታ ወደ ፖርቹጋል በ1504 ዓም የላከችው ዕሌኒ ነበረች፡፡ 

በአውሮፓ የነበረው ጸጋ ዘአብ የተባለው ሰው ለዳሚያኦ ዲ ጎይስ እንደነገረው ዕሌኒ ሁለት መጻሕፍትን በግእዝ ጽፋ ነበር(ስለ ቅድስት ሥላሴና ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም)፡፡ በወቅቱ ኢትዮጵያ ውስጥ በነበሩት ፖርቹጋላውያን መርጡለ ማርያምን እንደገና ያሠራቻት ዕሌኒ ናት፡፡ በ1527 ዓም ዐርፋ የተቀበረችውም እዚያው ነው፡፡ ባረፈች ጊዜ ኢትዮጵያ ውስጥ የነበረው አልቫሬዝ እንደሚለው በዕሌኒ ሞት መላ ኢትዮጵያውያን አዝነዋል፡፡ 

አያሌ ሰዎችም መርጡለ ማርያም ወደሚገኘው መቃብሯ እየመጡ ያለቅሱ ነበር፡፡ ሕዝቡም ‹እርሷ በመሞቷ ሁላችንም ታላላቆችና ታናናሾ ሞትን፤ እርሷ በሕይወት እያለን ሁላችንም በሕይወት ነበርን፤ እንጠበቅ ነበር፤ ማንም አይነካንም ነበር፡፡ እርሷ የሁሉም እናትና አባት ነበረችና› ይሉ ነበር፡፡

ፍራንሲስኮ አልቫሬዝ በመጽሐፉ ላይ ዐፄ ልብነ ድንግል በሐድያ ሡልጣኖች የእርስ በርስ ሽኩቻ ምክንያት ጣልቃ መግባቱን ይተርክልናል፡፡ በአሕመድ ግራኝ ጦርነት ጊዜ ሐድያዎች ከአሕመድ ግራኝ ጋር ወግነዋል፡፡ በኋላም ሐድያዎችና ኦሮሞዎች በንጉሥ ገላውዴዎስ ላይ ግንባር ፈጥረው ነበር፡፡ ገላውዴዎስ በድል ተወጥቶታል፡፡ ንጉሥ ሰርጸ ድንግልም ወደ ሐድያ በመዝመት በ1561 ሐድያዎችን ድል አድርጎ ነበር፡፡ ዐፄ ያዕቆብ የሐድያ ልጅ አጭቶ ነበር፡፡ ነገር ግን ጋብቻው ሳይፈጸም ዐረፈች፡፡

እንግዲህ ከ400 ዓመታት በፊት ሸዋ ትግራዮች፣ አምሐራዎች፣ አርጎባዎች፣ ጉራጌዎች፣ ጋፋቶች፣ ዳሞቶች፣ ኦሮሞዎች፣ አርጎባዎች፣ ሲዳማዎች፣ ጋሞዎች ሐድያዎችና ሌሎችም በእርሻ፣ በንግድ፣ በከብት ርባታ፣ በውትድርና፣ በመንግሥት ሥራ፣ በቤተ እምነት አገልግሎትና በሌሎቹም ተግባራት ወዲህና ወዲያ ሲሉባት የነበረች ቦታ ናት፡፡ በጊዜው ዐቅምና ጉልበት ያገኘ ያስገብራል፤ ሌላውም ተራውን እየጠበቀ ይገብራል፡፤ ዐቅምና ጉልበት ሲያገኝ ያምጻል፤ በተራውም ያስገብራል፡፡ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላው ቦታ መሄድ የተለመደ ነው፡፡

ታላቁ የታሪክ ሊቅ ፕሮፌሰር መርዕድ ወልደ አረጋይ እንደሚሉት ኢትዮጵያን ያዋሐዳት ፍልሰትና ዘመቻ ነው፡፡ በፍልሰቱ ሕዝቡ ከአንዱ ሥፍራ ወደ ሌላ ይጓዛል፡፡ መጀመሪያ ጥቂት በጥቂት፤ በኋላ ግን በሰው ሠራሽና ተፈጥሯዊ ምክንያቶች በብዛት ይፈልሳል፡፡ ዘመቻ ደግሞ አቅም ያገኘ ጉልበት የሰጠው ሌላውን ለማስገበር የሚሄድበት መንገድ ነው፡፡

መሬት የሁሉ ናት ባለቤት የላትም፤

ኃይለኛ እየሄደ ያስገብራል የትም፡፡

የሚለው አባባልም ከዚህ የመጣ ነው፡፡ በዚህ ዓይነቱ ዘመቻ ታሪኩ ቢመዘገብለትም ባይመዘገብለትም ያልተሳተፈ የኢትዮጵያ ማኅበረሰብ አልነበረም፡፡ ከዘመቻውና ከፍልሰቱ በኋላ ግን የራሱን ሥርዓት ዘርግቶ ወይም የሌሎችን ወርሶ ከሌሎቹ ማኅበረሰቦች ጋር አብሮ መኖሩን ይቀጥላል፡፡ ይዋለዳል፣ ይዛመዳል፤ ሥልጣንና ሀብትን እንደየባሕሉ ይጋራል፡፡

የኢትዮጵያን ታሪክ ያጠኑ ባለሞያዎች ኢትዮጵያ ውስጥ አንድም መጤ የለም፤ አንድም ሁላችንም መጤ ነን ይላሉ፡፡ የአንትሮፖሎጂ ሊቃውንት ኢትዮጵያን የሰው ዘር መነሻ ያደርጓታል፡፡ ስለዚህም ኢትዮጵያውያን ሁሉ ወደ ሌላ ሀገር ሄድን እንጂ እዚህ ሀገር ውስጥ ሁላችንም ባላገሮች ነን፡፡ ሰው በመነሻው መጤ አይሆንምና፡፡ በሌላ በኩል የታሪክ መዛግብትን ያጠኑ ሊቃውንት ደግሞ ኢትዮጵያ ውስጥ በነበረበት ጥንታዊ ርስት የጸና ሕዝብ እንደሌለ ይናገራሉ፡፡ ብዙዎቻችንም ከውጭ ወደ ኢትዮጵያ የገባን መሆናችንን መዛግብቱ ይገልጣሉ፡፡ በዚህ ካየነው ደግሞ ሁላችንም አሁን ላለንበት ቦታ መጤዎች ነን፡፡

ስለዚህም የሚያዋጣን ባለንበት ቦታ ተስማምተንና ተዋድደን፣ ተከባብረንና ተፈቃቅረን መኖር ብቻ ነው፡፡ እንደ አዲስ አበባ ያሉ ከዘመናት በኋላ በከተማነት የለሙ ቦታዎችን የእገሌ ብቻ ነው የእገሌ አይደለም ማለት ታሪካዊ ሞኝነት ነው፡፡ ጥንት የሁላችንም አልነበረም፡፡ ወይም የሁላችንም ነበረ፡፡  


በዚህ ዛሬ አዲስ አበባ በተቆረቆረችበት ሥፍራ ከአምስት መቶ ዓመታት በፊት ሁላችንም በኅብረት ስንኖር ነበር፡፡ አንዱ ማኅበረሰብ ኃይል ሲያገኝ፤ ሲገዛ፣ ሌላው ዐቅሙን አጠራቅሞ ሲገለብጠው፤ ሌላውም ሲስፋፋ፤ ሌላውም ሲመጣና ሲሄድ ኖረንባታል፡፡ 

ኢትዮጵያ ውስጥ ‹የእገሌ ብቻ› የሚባል ሥፍራ አለመኖሩን ጠለቅ ብለን ስንገባበት ታሪካችን ቁልጭ አድርጎ ያሳየናል፡፡ ሸዋ ደግሞ ለዚህ ጥሩ ማሳያ ነው፡፡

No comments