Latest

የኦሮማራ ትሩፋት የሆኑት አብንና ሊቀመንበሩ "ኦሮማራ የለም" ሲሉ ከማንም በፊት የራሳቸውን መኖር ነው የካዱት!! ስዩም ተሾመ



ስዩም ተሾመ

የኦሮማራ ዘመነ መንግስት የተጀመረው በዚህ ዓመት ከመሰላችሁ ተሳስታችኋል። ስለ ኦሮማራ ስርዖ መንግስት የአብን ሊቀመንበር ዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ በፌስቡክ ገፃቸው ላይ "ኦሮማራ የሚባል ነገር የለም፣ አልነበረም!" ብለዋል፡፡  

ካልተሳሳትኮ ዶ/ር ደሳለኝ የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ ባልደረባ መሰሉኝ፡፡ ታዲያ ባለፈው አመት ታህሳስ ወር ላይ በተዘጋጀው 2ኛው የኦሮማራ መድረክ በኦሮሚያና አማራ ክልል ከሚገኙ የተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የተወጣጡ ምሁራን ስለ ኦሮማራ ጥምረት ሲመክሩ አብን የሚባል ፓርቲ እና ዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ የሚባል ሊቀመንበር አልነበሩም፡፡  

ህወሓት የዘረጋውን የአፓርታይድ ስረዓት አሽመድምዶ ለመጣል በተደረገው ትግል ቁልፍ ሚና የነበረው የኦሮማራ ጥምረት መሆኑ የማይካድ ሃቅ ነው፡፡ ከዚህ ጥምረት በተሻለ አስተዋፅዖ አበርክቷል የሚል አካል ካለ ይውጣና እንከራከርበት፡፡  

ከዚያ በተረፈ ግን የአብን መመስረት ሆነ የዶ/ር ደሳለኝ ሊቀመንበርነት የኦሮማራ ቱርፋት ናቸው፡፡ ከዚህ አንፃር፣ የአብን ሊቀመንበር የሆኑት ዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ "ኦሮማራ የሚባል ነገር የለም፣ አልነበረም!" ማለታቸው የራስን ህልውና እንደ መካድ ነው፡፡  

ምክንያቱም ከኦሮማራ በፊት አብንም ሆነ ሊቀመንበሩ አልነበሩም!! ከኦሮማራ በኋላ ደግሞ አብንም ሆነ ሊቀመንበሩ አሉ፡፡ የኦሮማራ ጥምረት ባይፈጠር ኖሮ ልክ እንደ ቀድሞ አብን አይኖርም፣ ሊቀመንበሩም እንዲህ በይፋ ወጥተው በነፃነት አይናገሩም፡፡ 

ስለዚህ የአብን ሊቀመንበር "ኦሮማራ የለም፣ አልነበረም" ብሎ ሲናገር የራሱን መኖር ከመካድ የዘለለ ትርጉም የለውም፡፡ በመጨረሻም እኛ የኦሮማራ አቀንቃኞች ግን የአብን እና ሊቀመንበሩ በእውን እንዳሉ እናምናለን፡፡ ምክንያቱም መቼ፥ ለምን እና እንዴት እንደተፈጠሩ ጠንቅቀን እናውቃለንና!!

No comments