Latest

በእስራቴ ቀናት ከጎኔ ለነበራችሁ ሁሉ ፈጣሪ ዋጋችሁን ጨምሮ ይስጥልኝ - ጠበቃ ሄኖክ አክሊሉ ከእስር መልስ

ጠበቃ ሄኖክ አክሊሉ

በእስራቴ ቀናት ከጎኔ ለነበራችሁ ሁሉ ፈጣሪ ዋጋችሁን ጨምሮ ይስጥልኝ፤ ያለእናንተ ጉትጎታ የዛሬዋ ነጻነት በዘገየች ነበር። አሁንም በእስር ላሉ የአዲስ ወንድሞቻችን ድምጻችንን ማሰማት እንቀጥል።

እኛ የሸገር ልጆች ልደታ ተወልደን፣ ጨርቆስ አድገን፣ ጃንሜዳ ተጠምቀን፣ አኑዋር ሰግደን፣ መካነየሱስ ዘምረን፣ ቀበና ዋኝተን፣ ጉለሌ ተጫውተን፣ በቦሌ ኮረዶች ሙድ ይዘን፣ አዲስ ከተማ ተምረን፣ ዩንቨርስቲ ድንጋይ ወርውረን፣ ቡና/ጊዮርጊስ ደግፈን፣ ቄራ በሬ ገስተን፣ መርካቶ ተሰርቀን፣ መገናኛ ተጋፍተን ካሳንቺስ ላይ ወርደን፣ ጥቁር አንበሳ ታክመን፣ ከነማ መድሃኒት ገዝተን፣ ማዘጋጃ አልቅሰን፣ 3ተኛ ተመላልሰን፣ ጦላይ ታስረን፣ አንድነትን ተነጥቀን፣ ፍትህን ተነፍገን፣ በምርጫ ተገለን፣ ለፎቅ ተነስተን፣ ከግብርና ዘበኛ ሆነን፣ የአገሪቱን ታክስ ተሸክመን፣ አለን ተገፍተን።

ነገር ግን፣ ባለፉት 27 ዓመታት በወራሪዎች ተይዛ፣ እንደጠላት ግዛት ስትዘረፍ ለነበረችው አዲስ አበባ፣ የአብራኳ ክፋዮች ደርሰናል። እኔም ጥቅሟን ሕጋዊና ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለማስከበር የጀመርኩትን እንቅስቃሴ በበለጠ ሞራልና የጠራ ስትራተጂ እንደምቀጥልበት መግለፅ እፈልጋለሁ።


የህይወት ዕጣ ፈንታችን በእጃችን ውስጥ እንደሆነ አምናለሁ፤ የምንወስነውም እኛው ነን።

እንቅስቃሴያችንን ስናደርግ ግን የአዲስ አበባን ጂኦፖለቲክስ መገንዘብ ወሳኝ ነው። የኦሮሚያ ክልልና የፌደራል መንግስቱ በሕግ ያላቸውን መብትም አንዘነጋም።

እንግዲህ፣ አለን! እንኖራለንም!

No comments