Latest

ከራሱ ጋር ተጣልቶ እራሱ ላይ የሞት ፍርድ የፈረድ ጋዜጠኛ - ኬቨን ካርተር

ኬቨን ካርተር

መጋቢት 1993 ዓም ኬቨን ካርተር የተባለ ደቡብ አፍሪቃዊ የፎቶግራፍ ባለሙያ ሱዳን ውስጥ ተከስቶ በነበረው ርሀብ ከተባበሩት መንግስታት የእርዳታ ልኡክ ጋር ለበጎ አድራጎት ስራ ወደ ደቡብ ሱዳን ያመራል ፡፡  


በአንዷ መከረኛ እለትም ይህቺን ከታች የምትመለከቷትን ምስል በካሜራው አስቀረ፡፡

‹‹ርሀብ አድቅቆት የገዛ ራሱን መሸከም ያቃተው ህፃን ልጅ እና ይህን ህጻን ለመብላት የቋመጠ ጥንብ አንሳ›› የረሀብን ክፉ ገፅታ ፣የድርቅን አሰቃቂ ሁነት፣የምስኪኖችን እልቂት ፣ቃላት ሊገልፁ ከሚችሉበት አቅም በላይ በሆነ መንገድ በድንቅ ካሜራው ለአለም አስቃኘ፡፡ 

‹‹ቀጫጫ እጆች እንኳን ለመሮጥ፣ለመቦረቅ ይቅርና የገዛ አካሉን ለመሸከም ያዳገተው እግር፣ መቆም የከበደው ገላ እና በርሀብ በሞቱ ሰዎች የደለበ ፈርጣማ አሞራ!!››

ይህን ፎቶ ከወራት በኃላ በ 1993 ዓም ለኒውዮርክ ታይምስ ጋዜጣ ተሸጦ ታተመ፡፡ ምስሉ በመላው አለም ታየ፡፡ፎቶግራፈሩ፣ክብር እና ዝናን አተረፈ፡፡ ተሸለመ፣ተሞገሰ፡፡ዓለም ስለፎቶግራፈሩ አወራ፡፡

ከዚህ ሽልማት በኃላ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ በአንድ አስተዋይ ጋዜጠኛ የተወረወረች ያልተጠበቀች ጥያቄ ግን የህይወቱን አቅጣጫ እስከወዲያኛው ቀየረችው፤ አመሳቀለችው፡፡

‹‹ህፃኗ ልጅ እንዴት ሆነች….ታደግካት?!!>> አይኖቹ ፈጠጡ….ላብ አጠመቀው………ቃላት ከአንደበቱ ጠፋ!! በምናብ ወደ ደቡብ ሱዳንዋ የርሃብ መንደር ተሰደደ፡፡ ጠያቂው ግን ድጋሚ በጩኸት ጠየቀ ‹‹ህፃንዋን ልጅ ታደግካት ?? ነው ፎቶዋን ብቻ ነው ይዘኸው የመጣህ????›› ካርተር ጋዜጣዊ መግለጫውን አቋርጦ ወጣ፡፡  

ከወዳጅ ከዘመድ ሁሉ ተሰወረ፡፡ ከራሱ ጋር ተጣልቶ ለብቻው ውሳኔ አልባ ዶሴ ከፈተ፡፡ በገዳይዋ ፊት ጥሏት የሄደው የጎስቋላ ህፃን ነፍስ ለወራት እንቅልፍ ነሳው፡፡ ካርተር ራሱን ወነጀለ፡፡

የፎቶግራፍ ሽልማቱን ባሸነፈ በሦስት ወሩ በልጅነቱ ሲቦርቅ ባደገባት ‹‹ፓርክሞር›› በተባለች ለምለም ቀዬ በ33 አመቱ እራሱን ገድሎ ተገኘ፡፡ራሱን የሞት ፍርድ ፈረደበት ፡፡

No comments