Latest

የበጎ ሰው ሽልማትና የገጀራው ታሪክ !! (አሌክስ አብርሃም)

የበጎ ሰው ሽልማትና የገጀራው ታሪክ !!

በየአመቱ መሰለኝ የሚከበር የበጎ ሰው ሽልማት የሚባል ዝግጅት አለ ! ያው በተለያዩ ዘርፎች ጥሩ ስራ የሰሩ ሰዎችን መርጦ ይሸልማል ! የዘንድሮው የዚህ ፕሮግራም ስፖንሰር ታዲያ አንድ የአልኮል መጠጥ ፋብሪካ ነው !  


እንደሚታወቀው አገራችን ላይ ቤተሰብን በመበተን ፣ወጣቱን ሰካራምና ዋጋ ቢስ በማድረግ፣ በሱስ በየቤቱ የደነዘዘውን ትተነው ከነዚሁ ፋብሪካዎች ወደህዝቡ በገፍ የሚደፋውን አተላ ጠጥቶ በማሽከርከር በየቀኑ በትራፊክ አደጋ የሚያልቀውን ህዝብ ቤቱ ይቁጠረው!

 እንዲሁም ከሃይማኖታዊ ተቋማት እስከኪነጥበብ ዝግጅቶች በገንዘብ ሃይል በመያዝ ስለመጠጥ አስከፊነት እንዳይናገሩ አፋቸውን የሚያዘጉ <<የአመቱ መጥፎ ህዝብ ጨራሽ >> ድርጅቶ የአልኮል መጠጥ ፋብሪካዎች ናቸው ! እንግዲህ እነዚህ ናቸው ለበጎ ሰው ሽልማት ስፖንሰር የሆኑት !የአልኮል ፋብሪካዎች ቦርጭ እንጅ ሰበዊነትም አእምሮም አያሳድጉም !!

ይህ ነገር አንድ ሩዋንዳ ውስጥ የተፈጠረ ነገር አስታወሰኝ! አገሪቱ በገጠማት የእርስ በርስ ግጭት ያለቁ በርካታ ዜጎቿን ለመዘከር ወዲህም እንዳይደገም ለማስተማር ትልቅ ዝግጅት ታደርጋለች ! በወቅቱ ለዚህ ዝግጅት ከመንግስት ካዝና ከወጣው ገንዘብ በተጨማሪ በነገሩ ያዘኑ <<ይህ ግፍ አይደገም>> ያሉ በጎ አሳቢ ድርጅቶች ስፖንሰር ሆኑ!  

ዋነኛው ስፖንሰር ታዲያ አንድ መቀመጫውን በውጭ አገር ያደረገ የብረት አምራች ኩባንያ ነበር ! መድረክ ላይ የዚህ ድርጅት አርማ ኩፍስ ብሎ በዓሉ በተሰካ ሁኔታ ተከናዎነ ! በኋላ አንድ እሳት የሆነ ጋዜጠኛ ግን እሳት ለብሶና እሳት ጎርሶ እንዲህ ሲል በሳምንታዊ ጋዜጣ ጻፈ ! አንዳንዱ መቸም ዛሬ ላይ ሲጨፈር ነብሱ ነገንም ትላንትንም ትመለከት የለ !

<<በዛ አስከፊ ወቅት ምእራባዊያን በለገሱን ጥይት ከሞተው ሰው በማይተናነስ በገጀራ አንገቱ ተቀንጥሶ የተገደለው ወገናችን ቁጥር የትየለሌ ነበር ! የሚያሳዝነውና የሚያስገርመው እነዚህ በበዙ ሽህ የሚቆጠሩ ገጀራዎች በድብቅ ወደአገራችን የገቡት የትና በማን ተመርተው ይመስላችኋል ? ዛሬ ሰፖንሰር ሁኖ አብሮን በሚያለቅሰው የብረት ፋብሪካ !! >>

No comments