Latest

የአክሱም ሙስሊሞች ነገር! (አሌክስ አብርሃም)

የአክሱም ሙስሊሞች ነገር! (አሌክስ አብርሃም)

ሰሞኑን በአክሱም ሙስሊሞች ዙሪያ የማያቸው አስተያየቶችና ቪዲዮዎች እያስገረሙኝ ነው !! 


በተለይም አገራችን ላይ በበጎ ነገራቸው የሚጠቀሱ ፣ ሰለሰው ልጆች ነጻነት ሲጮሁ የከረሙ፣ሰለዲሞክራሲና እኩልነት ሰለፍቅርና ሰላም ሲሰብኩ የሚውሉ በርካታ ሰዎች የአክሱም ሙስሊሞች ጥያቄ ላይ ጭራሽ ተቃዋሚ ሁነው ሲከራከሩ አልያም ቃል ለመተንፈስ ሲተናነቃቸው እያየን ነው !! 

ነገሩ ከፖለቲካና እምነት ጋር ሰለተቀየጠ ላለመነካካት ጉዳዩን በጥንቃቄ እየተመለከቱት ይሆናል በሚል በጎ ትዝብት እንለፈውና ሰለጉዳዩ የተሰማንን እንነጋገር !

ብዙ ጊዜ በተለያዩ ሶሻል ሚዲያዎች ሰለሃይማኖቶች መቻቻል ሲሰበክ ተቃቅፈው የሚሄዱ ሙስሊምና ከርስቲያን ጓደኛሞች ፣ አልያም አብረው ቁመው የሚሳሳቁ ቄስና ሸክ ምስል መለጠፍ ይቀናናል ! መቻቻልና እኩልነት ማለት ሂጃብ የለበሰች ሴትና ጸጉሯን የለቀቀች ሴት አብረው መሄዳቸው አልያም መተቃቀፋቸው አይደለም!! 

መቻቻል ቄስና ሸክ ባንድ ሚኒባስ መሳፈራቸው አይደለም! መቻቻል ማለት ልዩነትን መቀበል መቻል ነው ! ቢያምህም እንዳንተ አይነተ እምነት የሌላቸው ሰዎች አንተ ልታዝባት በምትደፍርባት ምድር ላይ የማዘዝ የዜግነት ስልጣን እንዳላቸው ማመን ነው !!

አክሱም ከኢትዮጲያ ከተሞች አንዷ ናት !! ከተማ ማለት ደገሞ የአንድ እምነት አልያም የአንድ ፖለቲካ ፓርቲ ቅጥር ማለት አይደለችም !! ከተማ የተለያየ አመለካከት ፣ የተለያየ ባህል ፣ የተለያየ እምነት ያላቸው ሰዎች የሚኖሩበት የራሱ ጀኦግራፊያዊና ፖአለቲካዊ ወሰን ያለው ቦታ ነው !!

አክሱም ከተማ ናት ! አክሱም የኢትዮጲያ አንድ ከተማ ናት ! ሰለሆነች በኢትዮጲያ ህገ መንግስት የመተዳደር ግዴታ አለባት !! ህገ መንግስቱ ደገሞ ((መንግስት በሃይማኖት ሃይማኖትም በመንግስት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም)) ይላል!! ሰለዚህ ከተማዋን የሚያስተዳድራት መንግስት እንጅ ማንኛውም የሃይማኖት ተቋም ስላልሆነ ሙስሊሞችም ሆኑ የሌላ እምነት ተከታዮች ለሚያቀርቡት የቤተ እምነት ህንጻ ግንባታ ጉዳይም ሆነ ሌላ አስተዳደራዊ ጉዳይ መልስ መስጠት የሚችለው ብቸኛና ህጋዊ አካል መንግስት ብቻ ነው!!

ይህ በእንዲህ እንዳለ ከዚህ ጉዳይ ጋር ተያይዞ የሚቀርቡ ጉዳዮች ላይ አንዳንድ ነገር ማየት ይኖርብናል ! አንዳንዱ አክሱም በኢትዮጲያ የክርስትና መጀመሪያ ቦታ ሰለሆነች ቅዱስ ምድር ናት ሌላ ቤተ እምነት ሊገነባ አይፈቀድም ይላል! 

ጉዳዩ የቅድስናና ይጅማሬ ጉዳይ ከሆነማ እንኳን በኢትዮጲያ በዓለም የክርስትና እምነት የመጀመሪያ ቀድስት ስፍራ የምትባለው ኢስራኤል እንኳን ያውም ያን ያህል እስልምና ጠል አስተሳሰብና ሙስሊሞች ጋር የግዛት ሰጣ ገባ ውስጥ ሁና የተለያዩ እምነት ተቋማትን ግን አልከለከለችም ! በተለያዩ የክርስትና ተከታዮች ወንጌል ይሰበካል ሙስሊሞች በየመስጊዶቻቸው ይሰግዳሉ ወዘተ! ዙሮ ዙሮ አኢስራአኤልም ሆኑ ሳውዲ የምክንያታችን አካል ሊሆኑ አይገባም !!

ደግሞስ ቅዱስ ምድር ሰለሆነች በሚል ምክንያት ሌላ እምነት ተቋምን ከገፋች ቅድስናን የሚያረክስ ሰንት ነገር በውስጧ እንዲኖር አልፈቀድችም ወይ ? አክሱም ላይ አሸሸ የሚባልባቸው ጭፈራ ቤቶች ስንት ናቸው? በሴተኛ አዳሪነት ላይ ተሰማርተው ያሉ እነዚህኑ እህቶች የሚያስተናግዱ ቡና ቤቶች የሉም ወይ ? 

መጠጥ ቤቶቹስ እንደአሸን የፈሉት ተቀድሰው ነው? እውነት እናውራ ካልን ሌላም ከክርስትና ጋር እሳትና ጭድ የሆኑ መጽሃፉ በጥቁርና ነጭ <<እርም>> ያላቸው ሀዝቡ በባህል የሚፈጽማቸው ጉዳዮች አክሱም ላይ ሞልተዋል !!

ሌላው ወሃ የማይቋጥር ሰበብ መካ ላይ ክርስትና አይፈቀደም የሚል ነው ! መካ የአኢትዮጲያ አንድ አካል አይደለም! መካማ ሴት መኪና እንድትነዳ አይፈቀድም ነበርኮ ፣ መጠጥም አይፈቀደም፣ በዙ ነገር አይፈቀድም !እንደው እነሱ ያደረጉትን እናድርግ ከተባለ ደገሞ መተዳደሪያችንን ወደሸሪዓ መቀየር ነው !! ለማንኛውም እንደአገር የቆምነው እንደጎረቤት ለመኖር አይደለም!!

እና አክሱም እንደታሪካዊ ቅርስነት የእያንዳንዱ ኢትዮጲያዊ ሃብት ናት ! ሃውልቶቹ ቤተከርስቲያኖቹ ጭምር እንደቅርስ አገራዊ ሃብትነታቸው የሁሉም ኢትዮጲያዊ ነው !! መንግስታዊ እምነት እንደሌለ ሁሉ አንዲት ከተማም ከዚህ እምነት ውጭ ሌላው በየጓዳው ያምልክ ልትል ስልጣን የላትም ! 

አክሱምም ሆነ ሌሎች የኢትዮጲያ ከተሞች ላይ የማንኛውም እምነት ተከታይ በነጻነት የማምለክ ቤተ እምነቱን የመገንባት የሌሎችን መብትና ደህንነት በማይጋፋ መልኩ እምነቱ ጋር ተያያዥ የሆኑ ጉዳዮችን የመፈጸም ያልተሸራረፈ መብት አለው !!

No comments