Latest

👑 የእምዬ ምኒሊክ ዘመን ተሻጋሪ ተግባሮች (ከተክለ ጻድቅ መኩሪያ፣ ገጽ 583-599 የተወሰደ)

የእምዬ ምኒሊክ ዘመን ተሻጋሪ ተግባሮች

አጼ ምኒልክ አብዛኛውን የስልጣን ዘመናቸውን ያሳለፉት፣ በአገሪቱ 4ቱም ማዕዘን እየተዘዋወሩ ጸጥታ በማስጠበቅ፣ ከማዕከላዊ መንግስት ያፈነገጡ አውራጃዎችን መልሶ በመሰብሰብና ከኢጣሊያ ጋር ያለውን ውዝግብና ጦርነት በድልአድራጊነት እልባት በመስጠት ላይ ነበር፡፡  


ንጉሰነገስቱ ከአድዋ ድል በኋላ ሙሉ ትኩረታቸውን ስልጣኔና ልማት ላይ በማድረግ በርካታ ተግባራትን አከናውነዋል፡፡

ከምድር ባቡሩ፣ ከመንገዱና ከስልክ ማስገባት ወዲህ አሳባቸው በፍጹም ወደ አውሮፓ ትምህርት አዘነበለ፡፡ ከግብጽ እስክንድርያ ለመጀመሪያ ጊዜ. መምህራንን ቀጥረው በማስመጣትና ፕሮፌሰር ሐና ቤይ ሳሊምን በበላይነት በመሾም፣ ዛሮ በስማቸው የሚጠራውን ዳግማዊ ምኒልክ ት/ቤትን በ1900 ዓ.ም አቋቋሙ፡፡  

ቁጥራቸው 150 የሚሆኑ የመሳፍንት፣ የመኳንንትና የደሃ ልጆች ለመጀመሪያ ጊዜ በት/ቤቱ ገብተው መማር የጀመሩ ሲሆን፣ ለሌሎች አርአያ እንዲሆን አልጋወራሻቸው የሆነውን የልጅ ልጃቸውን ኢያሱንም በት/ቤቱ ገብቶ እንዲማር አድርገዋል፡፡

6ኛ አመቱን የጨረሰ ወንድና ሴት ልጁን ወደ ት/ቤት የማይልክ ወላጅ፣ ንብረቱ ባልተማሩት ልጆቹ ሳይሆን በመንግስት እንደሚወረስ አዋጅ አስነገሩ፡፡

የእጅ ስራ አዋቂዎችን የሚሰድቡ ሰዎች በአንድ አመት እስራት እንደሚቀጡ እንዲሁም በምስላቸው በ1894 ዓ.ም ለመጀመሪያ ጊዜ በፈረንሳይ አገር በመልካቸው ተዘጋጅቶ እንዲመጣ ባደረጉት የብርና ሽርፍራፊ የመገበባያ ገንዘብ ሳይሆን፣ በጥይት የሚገበያዩ ሰዎች፣ በያንዳንዱ ጥይት አንድ ብር እንደሚቀጡ አዋጅ በማስነገር የስልጣኔን በር የሚከፍቱ እርምጃዎችን ወሰዱ፡፡

ወታደሩ የባላገሩን ንብረትና ሚስት ከመንጠቅ ተቆጥቦ፣ ባላገሩ ካመረተው 1/10ኛውን ብቻ ለወታደሩ እንዲሰጥና ወታደሩ እራሱ አብስሎ እንዲመገብ በማወጅ፣ ባላገሩን ከውርደትና ከጥቃት አዳኑ፡፡ ከአድዋ ጦርነት በኋላ በመጡት በሞስኮብ ሐኪሞች እገዛ፣ በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆነውን የዳግማዊ ምኒሊክ ሆስፒታል አቋቋሙ፡፡

ቤተመንግስታቸውን በልዩ ልዩ ክፍል ከፋፍለው አሳምረው አሰሩ፣ መሳፍንትና መኳንንቱም በአዲስ አበባ የተለያዩ ስፍራዎች፣ በየስማቸው ያማሩ ቤቶችን እንዲሰሩ አደረጉ፡፡  

በቤተመንግስቱ ለመጀመሪያ ጊዜ የኤሌክትሪክ ብርሃን ሲያንጸባርቅ፣ ውሃ ከእንጦጦ በቧንቧ መጥቶ በቤተመንግስቱ ሲንፏፏ፣ እቴጌ ጣይቱ ለእንግዳ ማረፊያ ጣይቱ ሆቴልን ሲከፍቱ፣ ከ1878 ዓ.ም በፊት የአውሬ መፈንጫ የነበረችው አዲስ አበባ፣ ስልጣኔ የጀመረ መንግስት መዲና መሆኗን ማረጋገጥ ጀመረች፡፡

በዲፕሎማሲው መስክ ተቀማጭነታቸው አዲስ አበባ የሆነው የእንግሊዝ፣ የመስኮብ፣ የፈረንሳይ፣ የጣልያንና የጀርመን ሌጋስዮኖች እንዲቋቋሙ ተደረገ፡፡ በሚኒስቴር የሚመሩ ዘጠኝ የሚኒስቴር መ/ቤቶችንና በስራ አስኪያጅ የሚመሩ 2 የስልክና የፖስታ እንዲሁም የትምህርት ሚኒስቴር መ/ቤቶችን በአዋጅ በማቋቋምና ሚኒስትሮችንና ስራ አስኪያጆችን በመሾም በኢትዮጵያ የነበረው የአስተዳደር ስርአት ዘመናዊ እንዲሆን አድርገዋል፡፡

በከብት ጀርባና በእግር ይደረግ የበረውን እጅግ አድካሚ ጉዞ ለማስቀረት፣ በ1886 ዓ.ም ከጅቡቱ እስከ ሐረር፣ ከሐረር እስከ እንጦጦ፣ ከእንጦጦ እስከ ከፋና ከዚያም እሰከ ነጭ አባይ የባቡር መስመር እንዲዘረጋ የሚፈቅደው ውል እንዲፈረም አደረጉ፡፡ 

የባቡሩ መስመር በገንዘብ እጥረት እንደታቀደው እስከ ነጭ አባይ ባይሰራም፣ የተሰራው ክፍል የሚያልፍባቸው የከብትና የአውሬ መፈንጫ የነበሩት ደሳሳ ጎጆዎች የሚገኙባቸው ከሞጆ እስከ ድሬደዋ ያሉት በርካታ ቦታዎች፣ የደመቁ ከተሞች እንዲሆኑ የባቡር መስመሩ ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል፡፡

ምኒሊክ በ1889 ዓ.ም ከፈረንጅ አገር ሰራተኞች በደሞዝ በማስመጣት፣ በያገሩና በየወንዙ ብዙ ድልድዮችና መንገዶች እንዲሰሩ አድርገዋል፡፡ ጠላት አፍርሶት የነበረውን የአባይ ድልድይንም ሙሴ ሞሪስ ዶክፔና ዶ/ር ሚራብ የሚባሉ ባለሙያዎችን ልከው አሳምረው አስበጁት፡፡ የራስ መኮንን፣ የቀበናና የፍቅረማርያም ድልድዮች በአዲስ አበባ ተሰሩ፡፡

ከ1889 ዓ.ም ጀምሮ ሐረርንና ልዩ ልዩ አውራጃዎችን ከአዲስ አበባ የሚያገናኝ የስልክ መስመር በፈረንሳይ መሀንዲሶች እንዲዘረጋ በማድረግ፣ በ1892 ዓ.ም በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ በስልክ ማውራት እንዲቻል አድርገዋል፡፡ በኢትዮጵያ የመጀመሪያው አውቶሞቢል ወደ ኢትዮጵያ የገባውም በዳግማዊ ምኒሊክ ዘመን ነው፡፡

ዶ/ር ሚራብ የተባለው የምኒሊክ የረጅም ጊዜ ሐኪምና ረዳት፣ ምኒሊክ ከጠመንጃና ከመድፍ ይልቅ፣ በኤሌክትሪክ ሐይል የሚንቀሳቀስ የመካኒክ ሰራ የበለጠ እንደሚያስደስታቸው የጻፈ ሲሆን፣ ዊል ሒንዝ የሚባለው በአዲስ አበባ የብር ገንዘብ ይሰራ የነበረው ጀርመናዊ ደግሞ፣ ስራውን በሚሰራበት ጊዜ ምኒሊክ በቀን ከ3 ጊዜ በማያንስ ወደ ፋብሪካው በመመላለስ ስራውን ይቆጣጠሩና፣ አንዳንዴም እራሳቸው ቪስ በማዞርና ሞረድ በመሞረድ እርዳታ ያደርጉ እንደነበር ከሞቱ በኋላ ተናግሯል፡፡

በምኒሊክ ዘመን ተሻጋሪ ተግባሮች የተደሰተው የህብረተሰብ ክፍል፣ ስራቸውን በማድነቅ ደስታውን እንዲህ እያለ በግጥም ይገልጽ ነበር፣

ምኒልክና የኢትዮጵያ አንድነት፣ ተክለ ጻድቅ መኩሪያ፣ 1983 ዓ.ም፣ ገጽ 583-599 የተወሰደ

ኢትዮጵያዊነት ይለምልም

No comments