Latest

ምንድነው እንቆጳዊነት መቸስ ነው የእንቆጳ ትንሳኤ? (አሌክስ አብርሃም)

አሌክስ አብርሃም

ከሰሞኑ <<ዕንቆጳዊነት>> የሚል ሃሳብ መጀመሬ ይታወቃል ! በርካታ የፌስቡክ ወዳጆቸም ዕንቆጳዊነትን በገባቸው ልክ አልያም በራሳቸው በሰጣቸው ስሜት ልክ እየተቀባበሉት ይገኛሉ ! 


አንዳንዶች በጉዳዩ ላይ ሲያላግጡ ሌሎች ደግሞ ድግግሞሹ አስልችቷቸው አዲስ ጨዋታ አምጣ ሳምንቱን በዕንቆጳ ከረምክብን እያሉኝ ነው ! ከሆነስ ሆነና ምንድነው ዕንቆጳዊነት ? ማናትስ ዕንቆጳ ? የእንቆጳ ትንሳኤስ የእውነት ያስፈልገናል ወይ ? እነሆ እንቆጳዊነትን የጀመርኩበት ሃሳብ !

በክቡር ዶ/ር ደራሲ ሐዲስ አለማየሁ ከ 50 ዓመታት በፊት የተደረሰው ፍቅር እስከመቃብር መጽሃፍ ለብዙሃኑ ኢትዮጲያዊ ከልብወለድነት ያለፈ ትርጉም ያለው መጽሐፍ ነው!ያነበበውም ያላነበበውም ፍቅር እስከመቃብርን ያውቀዋል !! በዚህ መጽሐፍ የተፈጠሩ አይረሴ ገጸባህሪያት የአንድ ኢትዮጲያዊ የስጋ ዘመድ እንጅ ምድራችን ላይ ያልነበሩ የፈጠራ ገጸባህሪያት እስከማይመስሉ ተዋህደውናል!!

ከነዚህ ገጸባህሪያት አንዱ ጉዱ ካሳ (ካሳ ዳምጤ ) ነው! ጉዱ ካሳ ጉድ ከፊቱ ቀድሞ መጠሪያው የሆነው የማህበረሰቡን ጉድ ሳይፈራ ስለሚነቅፍ እና ከዘመኑ ወግ ባህልና ጎታች አስተሳሰብ ወጥቶ በወቅቱ ክነበርው ማህበረሰብ ያፈነገጠ ባህሪ ስለተላበሰ ነበር!!  

እንግዲህ ጉዱ ካሳ በናቱም ባባቱም ከባላባቶች የተወለደ <<በሁለት እጅ የማይነሳ የጌታ ዘር >> ነበር! ሁሉ በጁ ሁሉ በደጁ የሆነለት !! ምን ይሄ ብቻ በዘመኑ የቤተክህነት እውቀት የመጠቀ ሰው ነበር! ታዲያ እውቀቱ ተጨምሮበት ይቅርና ከወቅቱ ባላባቶች የዘር ሃረጉ በመመዘዙ ብቻ ስልጣን እና ወንበር ቢፈልግ ኖሮ የትየለሌ ይደርስ የነበርው ሰው ስልጣኑንመ ባጥንትና ዘር ያገኘውንም ክብር ጣጥሎት ማህበረሰቡን በትችት የሚያሽቆጠቁጥ ከባላባት እስከተራ ሰው ልክ ልካቸውን የሚነግር <<ጉድ >> ሆነባቸው! 

የሚኖርበት ማህበረሰብ በእውቀትና ማስተዋል ለገዘፈ እሱ ጠበበው ! የጠበበውን ማህበረሰብ አውልቆ ጥሎ በራሱ ዓልም በእርቃን ብቸኝነቱ ሲኖረ ማህበረሰቡ እብድ አለው ! ጉድ አለው!

ጉዱ ካሳ የሚኖርበት ማህበረሰብ ወግ ፣ህግ ና ስርዓቱ <<የማይረባ>> መሆኑን <<የማይጠቅም>> መሆኑን ይሰብክ ጀመረ! ይህን አሮጌ የበሰበሰ ስርዓት እንደእግዚአብሔር ቃል ሳይሻሻል ተከብሮ እንዲኖረ የሚጣጣሩትን የልማድ ባሮች ሁሉ <<ከብቶች>> <<ድንጋዮች>> እያለ ይዘልፍ ነበር!! እንዲህ ሲል

“የማኅበራችን አቁዋም የተሠራበት ሥራት፣ ልማዱ፣ ወጉ፣ ህጉ እንደ ሕይወታዊ ሥራት ማኅበር ሳይሆን ሕይወት እንደ ሌለው የድንጋይ ካብ አንዱ ባንዱ ላይ ተደራርቦ የላይኛው የታችኛውን ተጭኖ የታችኛው የላይኛውን ተሸክሞ እንዲኖር ሆኖ የተሠራ በመሆኑ ከጊዜ ብዛት የታችኛው ማፈንገጡ ስለማይቀርና ይህ ሲሆን ሕንጻው በሙሉ እንዳይፈርስ እንደገና ተሻሽሎ፣ ሰውን ከድንጋይ በተሻለ መልክ የሚያሳይ የሕያዋን አቁዋመ ማኅበር እንዲሠራ ያስፈልጋል”

ታዲያ እንዲህ በቁጭት ለተጨቆኑት (ለታችኞቹ ድንጋዮች ) ሲናገር <<አይ መበላሸት አይ መማር ከንቱ አይ የትልቅ ሰው ልጅ እያሉ ያዝኑለት ነበር!! እሱም በዛ በማይረዳው ማህበረሰብ ውስጥ ሰሚ የሌለው ጩኽቱ ወግና ባህል ያጠጠረው ተራራ ማህበረሰብ ጋር ተጋጭቶ ወደራሱ ሲመለስ ያዝንና ይበሳጭ ነበር!!ጉዱ ካሳ የሚናገርው ለማህበረሰቡ አይጥም ህብረተሰቡ የሚናገረው ለሱ አይጥመው ሀዝቡ እሱን <<ጉዱ>> እሱም ማህበረሰቡን <<የጫኑትን ተሸክሞ የሚግተለተል እንስሳ <የጉድ ማህበር >> እያለ አብረው ይኖራሉ !!

ይሄ በማህበረሰብቡ <<ጉድ>> የሆነ ጉዱ ካሳ ይህን ሁሉ ጉድ አልበቃው በሎ በመላስ የሚወጋው በድንዛዜ ባለማወቅ የሚወጋው ማህበረሰብ ጋር ጦር አውርድ የሚያስብል ሊላ ጦር ሰበቀ ! ይሄንኛው ጦረ ጭራሽ ዘመድ አዝማዱን <<አንገት ያስደፋ >> ማህበረሰቡም <<ለየለት>> በሎ በደንብ ይለየው ዘንድ የሚያደርግ ሆነና የጉዱ ካሳ ወትሮም የሌለ ማህበራዊ ሕይዎት ቀጭን ክሩ ተበጥሶ ማረፊያ ወደሌልው የባህል ገደል ገባ ! 


ምን አደረገ ? በወቅቱ አጠራር <<ባሪያ>> በሽልማት ተሰጠው ! የጥቁረቷ ነገር አይወራ ጸሃይ ዘወር ካለ አይንና ጥርሷ በቻ መነፈስ ላይ ብቻውን የተገጠመ መስሎ ይንቦገቦጋል እንጂ እሷ አትታይም ! <<ባርነት>> ለተባለ የመሃበረሰብ ክፉ እምነት እግዜር ተስማመቶ በጥቁር ቀለም ነክሮ ያጠመቃት የመሰለች የእኩለሌሊት ጨለማ !!

ለጉዱ ካሳ ተሰጠች! እግሩን እንድታጥብ ሲያገባ ለሚስቱን ጠብ ርግፍ ብላ እንድትገረድ ውሃ እንድትቀዳ እንጀራ እንድትጋግር እና ደግሞ ከፈለገም ወንድነቱ ካሰኘው በፈለገው ሰዓት ወደአልጋው ሊጎትታትም ይችላል <<ባሪያ ናት ሰው አይደለችም>> ለምሳሌ ውጭ በሌላ ነገር ተበሳጭቶ ሲመጣ እልሁ አልወጣ ቢለው ባገኘው ብትር እንደስልቻ ሊወቃትና እልሁን ሊያበርድባት ይችላል ከሞተችም ወይኔ ድብደባየን ሳልጨርስ ሞተች የማትረባ በሎ ሊቆጭ ይችላል ! <<ባሪያ ናታ ሰው አይደለችም>> ከወለደች ልጆቿም እሷም እኩል ባሪያ ናቸው!!

ጉዱ ካሳ ማህበረሰቡ <<ጨዋ የጨዋ ዘር የሆነች ደርባባ እመቤት አግብቶ በሚስቱ ግፊት <<ሰው ይሆናል >> ብሎ ሲጠብቀው እንቆጳን በደንቡ በወጉ ሚስቱ አድርጎ አገባት!! ያኔ እንኳን <<ጨዋው >> ማህበረሰብ <<ባሪያዎቹ >> ራሳቸው <<ኤዲያ አሁንስ እኒህ ሰውየ አበዙት ጭራሽ ባሪያ ያግቡ>> ሳይሉ አይቀሩም !! የማይታሰብ የማይሞከር ነዋ! እንቆጳ የጉዱ ካሳ ሌላ ህጋዊ ጉድ ሆነች ! 

ማህበረሰቡ ግን ጋብቻቸውን ማመን አልፈለገም !! እንቆጳ በገበያ የምትገፋ፣ ውሃ ልቅዳ ብትል እንደሳምራዊቷ ሴት አሳቻ ሰዓት ጠበቃ ወንዝ የምትወርድ፣ አገር ምድሩ ያሳቀቃት ከጓዳዋ ውጭ ሰው መሆን የከበደባት የባህል ጉድ የተሸከመች የጉድ ሚስት ሆነች! እንደሰባራ ቅል ካሁን ካሁን አውጥቶ ወረወራት ተበሎ ሲጠበቅ ትዳራቸው ጭራሽ አምሮበት ለጅ ለማፍራት በቁ !  

የእንቆጳ ትልቅ ህመም የሚጀምረው እዚህ ላይ ነው ሁለቱም ልጆቿን ሞት ነጠቃት ! ሞቱ የተፈጥሮው ሞት አልነበረም <<ከባሪያዋ እንቆጳ ዘራችን እንዳይቀጥል ዘር እንዳይበላሽ >> በሚል ሰበብ ምንም የማያውቁ ሀጻናት ለቆሸሸው የባህል ጣኦት መስዋዕት ሆኑ ! በምን ገደሏቸው ? ቢባል ብርቱው ጉዱ ካሳ ሳይቀር <<ጥላ ወጊ ነው ይላሉ ማመንም አለማመንም ከባድ ነው !! >> ብሎ ዝም ይላል!! 

እንቆጳዊነት ግን በምድሪቱ ወርድና ሰፋት የዘር ርሾውን ፣ የገፊና ተገፊ ቡኮውን አገር ምጣድ ላይ እየጋገረ ሚሊየኖችን በሰው ደም በሌሎችም መሸማቀቅና ሰቆቃ ላይ የግፍ ምድር ይገነባል !  

ጦሱ ብቻ ኣይደለም ራሱ ምከነያቱም ዛሬም አብሮን ተደላድሎ ተቀምጧልና እንቆጳዊነትን ሳይነቅሉ የበቀለበትን አኬልዳማ ምድር በመከባበር በፍቅርና እኩልነት ሳያርሱ ፍቅር ልዝራ ማለት ዘበት ነው ! እና እንቆጳዊነት ጥቁረት ነው? ዘር ነው? ቋንቋ ነው? ምንድነው? በየት በኩል ነው እየገፋ ገደል አፋፍ ሊያደርሰን የሚያቻኩለን?

ይቀጥላል!!

No comments