Latest

በወልቃይትና አላማጣ ነዋሪዎች ተፈናቀሉ! (ኢትዮጲስ ጋዜጣ)



ኢትዮጲስ ጋዜጣ

ወልቃይት እና ጠገዴ እንዲሁም ራያ አላማጣ አካባቢዎች ነዋሪዎች የማንነት ጥያቄ በማንሳታቸው ምክንያት ከመኖሪያ ቀያቸው እየተፈናቀሉ መሆኑ ተገለጸ፡፡


ከመስከረም 21/2011 ዓ.ም ጀምሮ ከትግራይ ክልል ወልቃይትና ጠገዴ አካባቢዎች፣ በአማራ ማንነታችን ምክንያት በትግራይ ክልል የህወሓት አስተዳደር የሚደርስብንን ግፍ ሸሽተን መኖሪያ ቀያችንን ለመልቀቅ ተገደናል በሚል አማራ ክልል ሶሮቃ ከተማ በመቶዎች የሚቆጠሩ ተፈናቃዮች በመጠለያ ጣቢያ እንደሚገኙ ታውቋል፡፡

ከተፈናቃዮች መካከል ለ10 ዓመታት የትግራይ ክልል ሚሊሽያ ሆነው እንዳገለገሉ የሚገልጹት አቶ አዳነ እሸቱ፣ ‹‹አማርኛ ቋንቋ ለምን ትናገራላችሁ? በአማርኛ ቋንቋ ዘፈን ለምን ትዝናናላችሁ?›› በሚል በመስቀል በዓል አከባበር ወቅት ነዋሪዎች ላይ ድብደባ እና እስር መፈጸሙን ተናግረዋል፡፡
 


አቶ አዳነ ከሌላው የሚሊሻ አባል አቶ ጥጋቡ አማረ እና ከበርካታ ነዋሪዎች ጋር ለ4 ተከታታይ ቀናት በበረሃ በእግራቸው ተጉዘው አማራ ክልል ሶሮቃ ከተማ መድረሳቸውን ገልጸዋል፡፡

‹‹እኔ ጠገዴ ወረዳ፣ ዳንሻ ከተማ፣ ከተማ ንጉስ ቀበሌ ነዋሪ ነኝ፡፡ በዚህ ቀበሌ መስቀል በዓልን ስናከብር፣ በአማርኛ ቋንቋ እንናገር፣ እንጨፍር ነበር፡፡ ይህንን የህወሓት ሰዎች አልወደዱትም፡፡
 


ወጣቶችን አሳደዷቸው፤ እኔንም ትጥቅ አስፈትተው ሊያስሩኝ ሲሞክሩ ህዝቡ ለምን ብሎ ጠየቀ፡፡ በህዝቡ ጣልቃገብነት ተርፌ ተሰደድሁ፡፡ ቀደም ብሎ ‹ከአማራ ህዝብ ጋር ጦርነት እንገጥማለን፣ ተዘጋጁ› ይሉን ነበር፡፡ እኛም ከህዝብ ጋር አንዋጋም፣ እኛም አማራ ነን ያልን የምንሻ አባላት እንደጠላት ተቆጥረን ቆይተናል›› ብለዋል አቶ አዳነ ተሾመ፡፡


ከተፈናቃዮች መካከል የ4ኛ እና የ5ኛ ክፍል ተማሪዎች የሆኑት፣ ዳንቸል ገብረ መድህንና አስፋው ክንፉ፣ ‹‹በምንማርበት ክፍል ውስጥ አማርኛ ቋንቋን ተናግራችኋል›› በሚል እንግልት ደርሶባቸው ተወልደው ካደጉበት አካባቢ መፈናቀላቸውን ተናግረዋል፡፡

ስለ ጉዳዩ የተጠየቁት የወልቃይት የአማራ ማንነት አስመላሽ ኮሚቴ ምክትል ሊቀመንበር የሆኑት፣ አቶ አታላይ ዛፌ በበኩላቸው፣ በርካቶች የአማራ ማንነታቸውንና ባህላቸውን በማንፀባረቃቸው የሰብዓዊ የመብቶቻቸው ተረግጦ በበረሃ መሳደድ፣ መፈናቀል እና እስራት ደርሶባቸዋል ብለዋል፡፡


በሶሮቃ መጠለያ ጣቢያ ውስጥ ለሚገኙ ተፈናቃዮች የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማህበር እና የአካባቢው ነዋሪዎች እርዳታ እያደረጉላቸው መሆኑን አቶ አታላይ አስረድተዋል፡፡ 

በተመሳሳይ በትግራይ ክልል ራያ አላማጣ ነዋሪዎችም የህወሓት ባለስልጣናት መሳደድና መፈናቀል እንደደረሰባቸው ታውቋል፡፡
 


የራያ ተወላጅ የሆኑት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር ዶ/ር ሲሳይ መንግስቴ እንደገለጹት፣ ከራያ አላማጣ እና ዋጃ አካባቢዎች መፈናቀል ደርሶባቸው ከ200 በላይ ሰዎች በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን በቆቦ ከተማ በመጠለያ ጣቢያ ይገኛሉ፡፡ 


የራያ ህዝብ የማንነት ጥያቄ በማንሳቱ ምክንያት ዋጃ እና አካባቢው መፈናቀል እና መሳደድ እየተፈጸመ እንደሚገኝ የገለጹት ዶ/ር ሲሳይ፣ በአካባቢው እስካሁን ትምህርት ቤቶች አልተከፈቱም ብለዋል፡፡ ‹‹የዋጃ እና አካባቢው ተማሪዎች አፍ በፈታንበት አማርኛ ቋንቋ ነው መማር የምንፈልገው በሚል ትምህርት አልጀመሩም፡፡ 


ይኸን ተከትሎ የአካባቢው የህወሓት ባለስልጣናት ወላጆቻቸው ላይ ማስፈራራትና ማዋከብ እየፈጸሙባቸው ነው፡፡ ይህ እየሆነ ያለው ከራያ ህዝብ የማንነት ጥያቄ ጋር ይያያዛል›› ብለዋል ዶ/ር ሲሳይ መንግስቴ፡፡

No comments