Latest

የብሮድካስት ባለስልጣን ቤቴልሄም ታፈሰና ኤልቲቪን ማስጠንቀቂያ ሰጠ! ስዩም ተሾመ

ኤልቲቪ

ከአንድ ሰዓት በፊት “የኤልቲቪ ጣቢያ ከብሮድካስት ባለስልጣን ማስጠንቀቂያ ተሰጠው” የሚል ጭምጭምታ ስሰማ ወደ ጣቢያው ስልክ በመደወል ሁኔታውን ለማጣራት ሞክሬያለሁ።  

በእርግጥ የተባለው ነገር እውነት ነው። አንድ የብሮድካስት ባለስልጣን ኃላፊ ወደ ጣቢያው በመደወል በአስቸኳይ ወደ ቢሮ እንዲመጡ ትዕዛዝ ይሰጣል። 

በመቀጠል “ጋዜጠኛ ቤቴልሄም ታፈሰ ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ሊቀመንበር ከዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ ጋር ያደረገችው ቃለ-ምልልስ "ለአንድ ወገን ያደላ ነው”፣ በዚህ ምክንያት የቴሌቪዥን ጣቢያው በብሮድካስት ባለስልጣን “የጥቁር መዝገብ” (Black List) መግባቱን፣ እንዲሁም የቴሌቪዥን ጣቢያው ቃለ-ምልልሱን ከኢንተርኔት ላይ በአስቸኳይ እንዲያወርድ የሚል ትዕዛዝ ሰጥቷል።  

ይህን ተከትሎ የጣቢያው ሰራተኞች ቃለ-ምልልሱን ለማውረድ ተገድደዋል። እዚህ ጋር መነሳት ያለበት ጥያቄ፤ ይህ የብሮድካስት ባለስልጣን ኃላፊ የስራ ኃላፊነትና ድርሻውን በሚያሳይ መልኩ የቴሌቪዥን ጣቢያው የተላለፈውን ደንብና መመሪያ በመጥቀስ በትክክለኛው አግባብ፥ በደብዳቤ ጉዳዩን ማሳወቅ ሲገባው ሰራተኞችን ቢሮ ጠርቶ የሚያስፈራራው እሱ ማን ስለሆነ ነው? 

የሃሳብና አመለካከት ነፃነት ተከበረ በተባለበት፣ ለብዙ አመታት ታግደው የነበሩ የሀገር ውስጥና የውጪ ሚዲያዎች በነፃነት እንዲንቀሳቀሱና ተገቢውን መረጃ ለህዝብ እንዲያደርሱ በሀገሪቱ ጠ/ሚኒስትር በይፋ በተፈቀደበት ወቅት፣ አንድን ሚዲያና ጋዜጠኛ በራሱ “ጥፋተኛና አድሏዊ” ብሎ ፈርጆ “ጥቁር መዝገብ ገብታችኋል” የሚያስፈራራው የሥራ ኃላፊ ኧረ እሱ ማን ነው?  

ጋዜጠኛ ቤቴልሄም ታፈሰ ከዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ ጋር ያደረገችው ቃለ-ምልልስ ተከትሎ ስነ-ምግባር በጎደላቸው ሰዎች የሥራ ስልኳ ፌስቡክ ላይ ሲለጠፍና በፀያፍ ስድብና ዛቻ ቁም ስቅሏን ስታይ ትንፍሽ ያላለ ዛሬ ደርሶ ትዕዛዝ ሰጪ የሆነው ማን ነው? 

አዎ… ይህ ሰው ትላንት ከቀድሞ የመስሪያ ቤቱ ኃላፊ ለኣይተ ዘርዓይ አሰግዶም ሲያጎበድድ የነበረ፣ አንድን የሚዲያ ተቋም ሆነ ጋዜጠኛ ለመፈረጅ ሙያዊ ሆነ የሞራል ስብዕና የሌለው ግለሰብ ነው።

No comments