Latest

ከአንቀልባ የማይወርደው ኦነግ (አንተነህ መርዕድ)

ከአንቀልባ የማይወርደው ኦነግ (አንተነህ መርዕድ)

በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ በርካታ ድርጅቶች ህዝባዊ አላማ አለን ብለው ተነስተው ከመፀነሳቸው የጨነገፉ፣ጎልምሰው የሞቱና ጤና እንዳጡ ያረጁ የኖሩትን ያህል፤ ኦነግ ግን እንደማያድግ ህፃን በአንቀልባ እንደታዘለ የኖረ ህፃን ቡድን ነው። ሲነሳ ፕሮግራሙን እንኳ በደባባይ አውጥቶ ማሳየት የማይችል፣ ዓላማው ለሌሎች ይቅርና ለራሱ አባላት እንኳ ግልፅ አድርጎ የማያውቅ ነው።

ቀድሞውኑ በአብዮቱ አፍላ ወቅት መኢሶንና ኢጨአትን በመሰሉ ድርጅቶች ጉያ ለማቆጥቆጥ ሲነሳ ድርጅቶቹ በደርግ ሲመቱ የሙት ልጅ (ኦርፋን) ሆነ። ቀጥሎም የሻዕብያና ወያኔ አላማቸውን የሚያስፈፅሙበት ዕቃ ሆኖ አረፈው።


በደርግ ጊዜ ሻዕብያ ጋር ሆኖ አሶሳ ላይ ያፈሰሰው የንፁሃን ደም ሳይደርቅ በ1983 ዓ ም በወያኔ አንቀልባ ታዝሎ በመጣበት ጊዜ በኢትዮጵያ ህዝብ በተለይም ቆሜለታለሁ በሚለው የኦሮሞ ህዝብ ላይ ትልቅ ወንጀል ሰርቶ ተልዕኮውን ሲጨርስ በአንቀልባ ታዝሎ ወጣ።

በበደኖው እልቂት፣ ካምፕ ወስጥ ትጥቃቸውን አስፈትቶ ለወያኔ ያስጨፈጨፋቸው የኦሮሞ ልጆች፣ በተወካዮች ምክር ቤት ውስጥ ያሉትን ሌሎች ድርጅቶች በመካድ ወያኔ ጋር በመተባበር በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ እንዲጫን ያደረጋቸው የጭቆና ህጎች ሁሉ እጁ አለበት።

አሁንም ታግሎ ሳይሆን ታዝሎ መጥቷል። የማንን ተልዕኮ ለማስፈፀም እንደመጣ የምናየው ይሆናል። ሶስት ዓመት ሙሉ በርካታ ወጣቶች በአጋዚ ስናይፐት በኦሮምያ ብቻ ወደ ሁለት ሺህ ወጣቶች በጠራራ ፀሃይ ሲገደሉ፣ እናት በልጆቿ ሬሳ እንድትቀመጥ ስትገደድ አርባ ዓመት ታጥቀናል ያሉ የዳውድ ኢብሳ ነፍጠኞች አንዲት ጥይት አልተኮሱም። የት ነበሩ? ከኢሳያስ ጉያ?

በ1983 ዓ ም የተበተነን ሰራዊት ሰብስበው ወታደር አለን ያሉት ኦነጎች በሰላሳ ዓመቱ ዛሬ ደግሞ ከኦህዴድ የተባረሩትን፣ የህወሃት ምንደኞችን ሰብስበው ወታደር አለን ብለዋል። ታዝለው መምጣታቸውን በመርሳት “ማን ነው የሚያስፈታን?” የሚል የጅል ህፃን ትዕቢት እያሰሙ ነው።

በዚህ የአዕምሮ ብስለት ደርጃ ላሉ የኦነግ መሪዎች የአሁኑን የኢትዮጵያ ህዝብ በተለይም ኦሮሞውን ለማወቅ በሚችሉበት ቁመና ላይ አይደሉም። የኢትዮጵያ ህዝብ እዚህ የደረሰው ጓዶቹን አሳልፎ ሰጥቶ ህይወቱን በስደትና በአገልጋይነት ባባከነ ቡድን ሳይሆን ዓላማውን አንግበው በወደቁ፣ በታሰሩ፣ በተንገላቱ ልጆቹ ነው። 

ይህንን ድሉንም ለነዚህ ከንቱዎች አሳልፎ አይሰጥም። ኦነግ ቆሜለታለሁ በሚለው የኦሮሞ ህዝብ በሚመጥን ደረጃ ከፍ እስካላለ ድረስ ወዳቂ ቡድን ነው። ለረጅሙ የትግል ህይወት ምስጋና ይግባውና የኦሮሞ ህዝብ አይደለም ለራሱ ለመላ ኢትዮጵያ ብሎም ለመላው የሰው ዘር ለመቆም የቆረጡ ልጆቹ ከመሃሉ እንደአሸን ፈልተዋል።

የሰው ህይወት በሚያጠፋ ብረት ሳይሆን ህይወትን በሚያለመልም፣ ሰውን በሚያሳድግ ሃሳብና አንደበት የአምባገነኖችን ምሽግ እየደረማመሱ ነው። ሁለት ሺህ የማይሞላ ክላሽ የታጠቀ ቡድን በኢትዮጵያ ውስጥ ፍትህን በማስፈን መሳተፍ ካልወደደ እንደተለመደው ሄዶ የኢሳያስን ፍየሎች መጠበቅ ይሻለዋል።

No comments