Latest

“የቆጡን አወርዳለሁ ብላ የብብቷን ጣለች” – አክሎግ ቢራራ (ዶር)



የጠ/ሚንስትር ዶር አብይ አህመድ መንግሥት የውጭ ምንዛሬውን ጭንቀት ለመወጣት ሲል ልዩ ልዩ የሕዝብ ኩባንያዎችን በከፊልና በሙሉ የመሸጥ ውሳኔ ሲያደርግ ውሳኔው በጣም ስላሳሰበኝ “Why the Rush?” የሚል ዘገባ አቅርቤ ነበር። በተጨማሪ፤ በVOA በአማራ ድምጽ ተመሳሳይ ትንተና አቅርቤ ነበር። አገራችን የገጠማት ህወሓት ሰራሽ ሁለገብ ችግር ይገባኛል። የውጭ ምንዛሬ ቀውስ እንዲሁ የተከሰተ አይደለም። በእድገቱ ዙሪያ የባከነውና የተሰረቀው የውጭ ምንዛሬ የሚያስደነግጥ መሆኑን ለብዙ ዓመታት ስጠቁም ቆይቻለሁ።

የህወሓት ባለሥልጣናትና ተባባሪዎቻቸው ልዩ ልዩ ምክንያቶች እየፈለጉ ወደ ውጭ አገሮች በመሄድ ያባከኑትና የደበቁት ብዙ ቢሊየን ዶላር ለስራ አይደለም። በውጭ የደበቁትን ግዙፍ ኃብት ለመከታተልና ሃብት ለመደበቅ ጭምር ነው። እድገት ለግል ጥቅም ተነግዶበታል ብል የተሳሳትኩ አይመስለኝም። የተሰረቀውና የባከነው የውጭ ምንዛሬ ልዩ ልዩ ፋብሪካዎችን ሊሰራ ይችል ነበር፤ የስራ እድል ይፈጥር ነበር። ፍላጎትን ለማሟላት የሚችሉ ኩባንያዎችን ለመመስረት ያስችል ነበር።

በቅርቡ ቢሊየኔርና ሚሊየኔር የሆኑትን፤ ኃብታቸውን ደብቀው በውጭ ባንኮች የደበቁትን ግለሰቦች ዝርዝር በሜዲያ ስመለከት፤ እነዚህ ግለሰቦች ብቻ ከ$28 ቢሊየን በላይ በውጭ ባንኮች ደብቀዋል። ኢትዮጵያንና የኢትዮጵያን ሕዝብ የሚያፈቅርና የሚያከብር ቡድን ይኼን ወንጀል አይፈጽምም፤ ህሊናው አይፈቅድለትም በሚል እጀምራለሁ።

ይህ ከኢትዮጵያ ሕዝብ የተሰረቀና ከአገር የሸሸ ግዙፍ ኃብት በውድም ሆነ በግድ መመለስ አለበት።
አፍሪካዊያን እንዲህ ይላሉ። “አንበሳው የራሱን ታሪክ እስከሚናገር ድረስ፤ አዳኙ የበላይነቱን ይዞ፤ ራሱን በማመስገንና በማሞገስ ታሪክ ሰራሁ እያለ ይፎክራል።” ህወሕቶች አስደናቂ እድገት አሳየን፤ በራሳችን ጥረትና ፍጥረት ኃብት ያዝን የሚሉት ከዚህ ጋር ተመሳሳይነት አለው። የሌላውን መብት አፍነው አፋኞቹ ታሪክ ይፈጥራሉ፤ ያልሰሩትን የእድገት ውጤት ሰራን ይላሉ፤ የሰረቁትን ይክዳሉ።

ጥናቶች የሚያሳዩት ግን፤ የነሱ ታሪክ የፈጠራና የሌብነት ታሪክ መሆኑን ነው። አንበሶች ነጻነታቸውን አውጀው መነጋገር ሲጀምሩ ህወሓቶች የለመዱትን እልቂትና ግፍ ሊቀጥሉበት ይሞክራሉ። አንበሶች የምለው የኢትዮጵያን ሕዝብ፤ በተለይ ወጣቱን ትውልድ ነው። “ባንተባበር ይበሉን ነበር” እያሉ፤ በአንድነት፤ ለአንድ አገር፤ ለአንድ ሕዝብ ነጻነት፤ ፍትህ፤ ሰብአዊ መብትና ዲሞክራሳዊ፤ ለዘላቂና ፍትሃዊ እድገት የሚያካሂዱት ትግል አስደናቂና ታሪካዊ ነው። ለውጡ በምንም አይነት ሊቀለበስ አይችልም።

የሚያዋጣው ለውጡን እየደገፉ ገንቢ የሆኑ አማራጮችን ማቅረብ ነው። የዚህ ሃተታም ምክንያት ይኼው ነው።
ዶር አብይ አሕመድ ጠቅላይ ሚንስትር ከሆኑበት ጊዜ ጀምሮ ለኢትዮጵያና ለ110 ሚሊየን ሕዝቧ የሚያደርጉት “የነብር ሩጫ” የመሰለ የለውጥ ፍጥነት እንዴት ተስፋ እንደሰጠኝ በቃላት ለመግለጽ አልችልም። ከነዚህ መካከል እጂግ በጣም ያስደሰተኝ ከዚህ በፊት ምንም ዋጋ ተሰጥቶት በማያውቀው በኢትዮጵያዊያን ነጻነት፤ ሰብእነትና የህይወት ብርቀኝነት ላይ ያደረጉትና የሚያደርጉት ትኩረት ነው። እኛ ኢትዮጵያዊያን ለእያንዳንዳችን ሰብእነት ዋጋ ካልሰጠነው ማንም ዋጋ አይሰጠውም። 

ሌላው ዓለም አያከበረንም፤ እንዲይውም ይንቀናል። እኒህ ወጣት መሪ፤ እነዚህን፤ ህወሓት መራሹ ስርዐት ለማውደም ቀን ከሌት የታገለባቸውን፤ የኢትዮጵያንና የኢትዮጵያዊነትን መዐከልነትንና ወሳኝነትን፤ የሰብአዊ መብቶችንና የዲሞክራሲን አስፈላጊነትን ማስቀደማቸው ራሳቸውን ከሌሎች ቀደምት መሪዎች ይለያቸዋል። ያስተጋቧቸው እሴቶች ለዘላቂና ለፍትሃዊ እድገት መሰረት ናቸው። ራእይና ተልእኮ ከእነዚህ እሴቶች ውጭ የማይሰሩ መሆናቸውን ባለፉት ሃያ ሰባት ዓመታ አይተናል። እኒህ መሪ ከሕዝቡ የሰሙት የፖሊሲ ጥያቄ እድገት የዜጎችን ህይወት ካላሻሻለ ፋይዳ ቢስ ነው የሚል ይዘት አለው። በኔ ግምት እኒህ መሪና የተለሙትን ፍትሃዊ መድረሻ የሚደግፉ ብዙ መቶ አብዪች ያስፈልጋሉ፤ እሳቸውን ብቻ እንደ መሳያ ብናመልካቸው ሸኩሙን አይችሉትም።

በተጨማሪ፤ ሌሎች ሸክሞች በሌላ መንገድ ሚና እንዳይኖራቸው ጥንቃቄ መደረግ አለበት።
ከአሁን በኋላ፤ የሁሉም ኢትዮጵያዊያን ትኩረት ጠንካራ ብሄራዊ ተቋሞችን መስርቶ ድህነትን፤ ኋላ ቀርነትን፤ ሌብነትን፤ ስግብግብነትንና ጥገኝነትን በጋራ ቀርፎ ነጻ፤ ታላቅና ኃብታም የሆነችን ኢትዮጵያ መመስረት ነው። በኔ እምነት ከተባበርን፤ ሌብነትንና ዘረኝነትን ካጠፋን ይኼ ይቻላል።

ኢትዮጵያ እንደ ሌሎች አገሮች አይደለችም። ረዢምና አስደናቂ ታሪክ አላት። አቀማመጧ የማይገኝ በረከት ሰጥቷታል። የሕዝብ ስርጭቷ ያስቀናል። የቅኝ ገዢዎች መንፈሷን አልሰበሩትም። ሆኖም፤ ባለፉት መቶ ዓመታት ነጻነቷን፤ ሉዐላዊነቷንና የሕዝቧን አንድነት ለማስከበር፤ በጦርነት የደከመች፤ ባለፉት ሃያ ስምነት ህወሓት መራሽ ዓመታት በብሄርና በቋንቋ የተከፋፈለች፤ ጥቂት የስርዓቱ ልሂቃን በሕዝብ ስም ካዚኖ አድርገው የተቀራመቷት አገር ናት። ልክ እንደ ነብር የሚሮጡት ጠ/ሚንስትር የደከመውንና የተመዘበረውን ኢኮኖሚ እንዲያንሰራራ ለማድረግ የጀመሩት ራእይና ግብ መልካም ነው። የኢትዮጵያ የእድገት አቅጣጫ አገር ተከል እንጅ የተውሶና ጥገኛ መሆን

የለበትም። ጠቅላላ የአገር ገቢ ጨምሯል የሚለው የህወሓት መራሹ ቡድን ፕሮፓጋንዳ ለአብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ ኑሮ መሻሻል አስተዋጾ አላደረገም።

የአብይን ተስፋ የሚሰጥ አቅጣጫ ስኬታማ ለማድረግ ግን መሰረታዊና ተቋማዊ ለውጥ ያስፈልጋል። ተግዳሮቶች የተወረሱት አሁንም የበላይነቴ ይጠበቅ ከሚለው ከህወሓት መራሹ ስርዓት ነው። ይህ ቡድን በገፍ በሌብነት የሰበሰበው ኃብትና ንብረት፤ ከአገር ያሸሸው የውጭ ምንዛሬ በኢትዮጵያ ታሪክ ብቻ ሳይሆን ድሃና ጥገኛ በሆኑ በሌሎች አገሮች ታይቶና ተሰምቶ አያውቅም። ይህ ድርጅታዊ ምዝበራና አይን ያወጣ ሌብነት ያሳየኝ፤ ሌቦቹ ኢትዮጱያንና የኢትዮጵያን ሕዝብ የማያፈቅሩ መሆናቸውን ነው።

እድገት መኖሩን እየተቀበልኩ፤ ዛሬ የተከሰቱት የኢኮኖሚ፤ የባጀት፤ የባንክ አገልግሎት፤ የውጭ ምንዛሬ እጥረትና ሌሎች የፖለቲካ ኢኮኖሚ መስፈርቶች ችግሮች ችግሩን በፈጠረው በህወሓት መራሹ ስርዓት አይፈቱም የሚል ጽንሰ ሃሳብ አቀርባለሁ። ተቋሞች ወሳኝ ሚና ስለሚኖራቸው፤ ከፓርቲና ከመንግሥት የበላይነት ወደ ተወዳዳሪ፤ አምራችና ተደጋጋፊ ኢኮኖሚ ለመሸጋገር ግልጽነትና ሃላፊነት የሚያሳይ የኢኮኖሚ፤ የፋይናንስ፤ የባንክ፤ የባጀት፤ የውጭ ምንዛሬ አጠቃቀም፤ የውጭ መዋእለንዋይ ፈሰስ፤ የግል ተሳትፎና የገበያ

አመራር ሕግ፤ ደንብና አሰራር (Regulatory Framework) መኖር አለበት:፡
ህወሕት መራሹ አገዛዝ የሚታወቀው በእነዚህ እሴቶችና አቅጣጫዎች ሳይሆን ሰብእነትን፤ ሰብአዊ ክብርን፤ ፍትህን፤ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን ዝቅ በማድረግ ነው። ይህ ስርዓት እያንዳንዳችን ወደታች ወስዶናል። የኢኮኖሚውን ምርታማነት አፍኖታል። የውጭ ምንዛሬን አባክኖታል። ባንኮችን አክስሯቸዋል። የግል ክፍሉን ተወዳዳሪና አምራች እንዳይሆን ጫና አድርጎበታል። 

የመዋዕለንዋይ ፈሰስ ወደ አገር ተከል አምራችነት እንዳይሸጋገር ባደረገ ሁኔታ ፈሰሱ በአጭር ጊዜ ትርፍ ወደሚያስገኙ፤ የህንጻ፤ የቤት ስራ፤ የሆቴልና የምግብ አገልግሎት፤ የፍጆት ንግድ ስራዎች እንዲዞር አድርጎታል። የተሰሩት ግንቦች፤ ድልድዮች፤ መንገዶች ጥራታቸው ዝቅተኛ ስለሆነ አገሪቱ በማትችለው መጠን ለጥገና ብዙ ቢሊየን ብር ፈሰስ ይሆንል። ፈሰስ ሲሆን ሌብነት አብሮ ያድጋል፤ ተጠያቂ የለም።

እዚህ ላይ የማስጠነቅቀው ከህወሓት ውጭ ያሉ የፖለቲካ ልሂቃን ችግሩ የአፈጻጸም እንጅ “የልማታዊ መንግሥትና የብሄር ተኮር ፌደራሊዝም አይደለም” ይሚሉትን ነው። “ ልማታዊ መንግሥት” በህወሓትና አጋሮቹ የተጀመረ አይደለም። ሁሉም መንግሥታት ልማታዊ ሚና አላቸው። ፌደራሊዝም አግባብ አለው። ብሄር ተኮሩ ፌደራሊዝም በምንም አይነት ከግለሰቦች መብትና ከኢትዮጵያዊነት ጋር አብሮ አይሄድም። ይህ ሞዴል ግጭት ፈጣሪ ነው። ሌብነትን አጠናክሯል። መቀየር አለበት። ያለውን ስርዓት እንደ ኃይማኖት

እያመለኩ መጓዝ አያዋጣም። ህወሓታዊ መስመር ነው።
ስለዚህ፤ ጠ/ሚንስትሩ የጀመሩት የለውጥ ሂደት በቀላሉ መታየት የለበትም። እኔም ሆንኩ ሌሎች አገር ወዳዶችና ለፍትህ፤ ለእውነተኛ እኩልነት፤ ለሕግ የበላይነት፤ ለዘላቂና ፍትሃዊ እድገት እና ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ስንታገል የቆየን ሁሉ ይህን አዲስ ምእራፍ እየደገፍን ገንቢ የሆኑ የፖሊሲ አማራጮችን ለኢትዮጵያና ለመላው ሕዝቧ ጥቅም እንዲሆን የማቅረብ ግዴታ አለብን። ይህን ለማድረግ መደራጀት አስፈላጊ ነው። ስር የሰደደ፤ አዲስ ተጠቃሚዎችን የፈጠረ መዋቅርን ለመለወጥ የሕዝብ ተሳትፎና ድጋፍ ወሳኝ ነው።

በዚህም መንፈስ የኢህአዴግ መንግሥት በቅርቡ “የመንግሥት/የሕዝብ” የነበሩትን ግዙፍ የሆኑ ድርጅቶች በከፊልና በሙሉ የግል ለማድረግ የወሰነው ፖሊሲ “የቆጡን አወርዳለሁ ብላ የብብቷን ጣለች” እንዳይሆን ከፍተኛ ስጋት አለኝ። እርግጥ ነው፤ አፍሪካዊያን እንደሚሉት “መብረቅ ሲሰማ ዝናብ” ዘነበ ማለት አይደለም። አዋጅ ሲወጣም ስራ ላይ ዋለ ማለት አይደለም። ጥናትና ውይይት እንደሚደረግበት እገምታለሁ። ግን መብረቅ ሰምቶ ጥንቃቄ አለማድረግ ይጎዳል። ጥናት፤ ምርምርና አማራጮችን ማጤንና ማቅረብ ያስፈልጋል።

ጠ/ሚንስትሩ እንዳሉት የውጭ ምንዛሬ ችግር አለ፤ ይህ ችግር አሁን አልመጣም፤ የቆየ ችግር ነው። ስርዐት ወለድ ነው። ከዚህ በፊት ዓለም ባንክና አይ ኤም ኤፍ በተደጋጋሚ አሳስበው ነበር። ሁለቱም ድርጅቶች የውጭ ምንዛሬ ሌብነትና መባከን አለ የሚል የውስጥ ዘገባ አቅርበዋል።

ይህን ግዙፍ ችግር ለመወጣት ልዩ ልዩ ዘዴዎች መጠቀም ይቻላል፤ ለምሳሌ ወዳጅ አገሮች ነጻ ድጎማ እንዲያደርጉ፤ ዲያስፖራው የውጭ ምንዛሬ እንዲልክ እገባውን ሙሉ በሙሉ ማቆም፤ በገፍ የሚሸመተውን የቅንጦት እቃ ማቆም፤ ቢያንስ መቀነስ፤ የውጭ ኢንቬስትመንት እንዲጨምር አግባብ ባለው መንገድ ማመቻቸት። ወደ ውጭ የሚላከው እቃ አንደ ድሩው እንዳይሰረቅ ማድረግ ወዘተ። ሆኖም፤ የአጭር ጊዜን የውጭ ምንዛሬ ችግር የረዢም ጊዜን ብሄራዊና መዋቅራዊ ቀውስ እንዳያመጣ ጥንቃቄ መደረግ አለበት።

ይህን ችግር በማጤን፤ በተለይ ትኩረት ልሰጠው የምፈልገው ለኢትዮጵያና ለሕዝቧ የሚጠቅመው አማራጭ የትኛው ነው የሚለውን ነው።
የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ አመራርና መዋቅር የችግሩ መንስኤ ነው።

የኢትዮጵያ “አስደናቂና ፈጣን” እድገት ሞተሮች ተብለው የሚጠሩት ህወሓት መራሹ ፓርቲ፤ በተለይ ህወሓትና የፈጠራቸው እንደ ኤፎርት ያሉ ድርጅቶችና መንግሥት የሚያንቀስቀሳቸው የዘመናዊ ኢኮኖሚ ክፍሎች ናቸው። እነዚህ ክፍሎች የሚይሳዩት የኢኮኖሚን

ቀፎነት ነው። ከስድሳ እስከ ሰባ በመቶ የሚሆነውን ዘመናዊ ኢኮኖሚ የሚቆጣጠሩት ህወሓቶችና የህወሓት አጋር ድርጅቶቹ ናቸው። ይህ የበላይነት ለሌብነት አመች ሁኔታዎችን ፈጥሯል። ከዚህ የተከተለው የውጭ ምንዛሬ ምዝበራው ግዙፍ ነው። ሌላው ቀርቶ፤ በሴንሲቲቭ ጉዳዮች ላይ ዱዳ የሆነው አይኤምኤፍ ጉዳዩ ስላሳሰበው በጥቂት ዓመታት ብቻ $ 11 ቢሊየን ተሰርቆ ከአገር እንደወጣ ተናግሯል። በማንኛውም መስፈርት ስከታተለው የኢትዮጵያ ሕዝብ የተሸከመውን ሸክም በይቅርታ ማለፍ አይቻልም።

የግል ክፍሉ ጫጩትና ደካማ የሆነበት ዋና ምክንያት ህወሓት መራሹ ቡድን ስላፈነው ነው። የዚህ አሉታዊ ውጤቶች ብዙ ናቸው። የግሉ ክፍሉ ጫጩት ነው፤
  1. የስራ እድል የለም፤ የተዛባ የገቢና የኑሮ ሁኔታ ይታያል፤
  2. የዋጋ ግሽፈት አደገኛ ደረጃ ላይ ደርሷል፤
  3. የውጭ እዳ አገሪቱ ለመክፈል ከማትችልበት ደረጃ በላይ አድርሷታል፤
  4. ፍላጎትና አቅርቦት ሊመዛዘኑ አልቻሉም፤
  5. ከውጭ የሚሸመተው ዋጋ፤ ከአገር ወደ ውጭ ከሚላከው ዋጋ፤ ከአስራ ስምንት እጂ ጊዜ በላይ ይሆናል፤
  6. የሚሸመቱ የድሎት እቃዎች ከሚሸመተው የማምረቻ እቃዎች ይበልጣሉ፤
  7. የብር ጥቅም ዋጋ አጥቷል፤ በደርግ መንግሥት 1 ብር አንድ ዶላር ይገዛ ነበር፤ ዛሬ የሚገዛው ሃያ ሰባት ብር አንድ ዶላር ነው፤
  8. ፈጣን እድገት አለ ቢባልም የኢኮኖሚው መዋቅር ከጥንቱ አልተሻሻለም፤
  9. አብዛኛው የኢኮኖሚ ክፍል የገጠር ነው፤ ይህ ወሳኝ ኢኮኖሚ ዘመናዊ አልሆነም፤ አንዱ የመዋቅር ችግር ይኼው ነው፤
  10. አገሪቱ ወደ ውጭ የምታቀርበው እቃ አሁንም የኢንዱስትሪ ውጤት አይደለም፤ ቡና፤ ሰሊጥ፤ ቆዳ ወዘተ፤ በስፋትም ሆነ በጥራት የውጭ ንግድ ሚዛናዊ አልሆነም፤
  11. የውጭ ምንዛሬ ባክኗል፤ አንድ ባለሥልጣን ወደ ውጭ ሲሄድ ሻንጣውን በውጭ ምንዛሬ ሞልቶ ለሆቴል በቀን ከአንድ ሽህ አምስት መቶ ዶላር በላይ የከፈለበት ሁኔታ አለ፤
  12. የውጭ ምንዛሬ እጥረት የተለመደ ቢሆንም፤ የኢትዮጵያን እንቆቅልሽ የሚያደርጉት ብዙ ክስተቶች አሉ፤ ከእነዚህ መካከል በገፍ ከአገር በሌብነት ወይም ከሕግ ውጭ የሚሸሸው (Illicit Outflow of Capital) ኃብት ብዛት አሳሳቢ ደረጃ የደረሰው ከብዙ ዓመታት በፊት ነው፤
  13. በዓመት $3 ቢሊየን፤ እስካሁን በዝቅተኛ ተመን $30 ቢሊየን እስከ $40 ቢሊየን ተሰርቆ ከአገር ወጥቷል፤ ይኼ ከፍተኛ ወንጀል ስለሆነ ራሱ አንድ የትንተናና የፖሊሲ አርእስት ነው፤
የባንክ እና የውጭ ምንዛሬ ተበዳሪዎች እነማን ናቸው ብየ ራሴን ስጠይቅ፤ በአብዛኛው የመንግሥት እና የህወሓት ኩባንያዎች ናቸው፤ በተለይ እንደ ኤፈርት ያሉ ህወሓት የፈጠራቸው ኩባንያዎች፤ የመንግሥትን ከፓርቲው ለመለየት አልችልም፤ ሁለቱ አንድ ሆነው የሰሩባቸው ሁኔታዎች አሉ፤ ለምሳሌ፤ ሜቴክ የመንግሥት ይሁን እንጅ የበላዮቹ ህወሓቶች ናቸው፤ ከባንክ ተበድሮ ብዙ ቢሊየን ብር አባክኗል። ለስኳር ምርት ተበድሮ ስኳሩም የለ፤ ገንዘቡም ተሰረቀ። በሃላፊነት የሚጠየቀው ማን ሊሆን ነው?
የውጭ መዋእለንዋይ፤ በግልጽነት፤ በሃላፊነት፤ በተሳታፊነት አይሰራም፤ “ጅቦች” ተብለው የሚጠሩት፤ ከአገር ውስጥ ተጠቃሚዎችና ከአቀባባይ ከበርቴዎች ጋር ጠንካራ ቁርኝት ፈጥረዋል እና፤ የኢትዮጵያ የግል ክፍል ከኢኮኖሚው ጨዋታ ውጭ እንዲሆን ተደርጓል።

ባጭሩ፤ “አብዮታዊ ዲሞክራሲና እድገታዊው መንግሥት” የፈጠሩት የኢኮኖሚ መርህ ለነጻና ለተወዳዳሪ ገበያ ዋናው ማነቆ ሆኗል። የኢኰኖሚና የፍይናንስ ቀውሶች ከሰማይ አልወረዱም፤ ሰው ሰራሽ፤ ስርዓት ሰራሽ ናቸው። አዲስ ተጠቃሚዎች አሉ፤ ከእነዚህ የተገለሉና በእነዚህ የተጎዱ አሉ። በተለይ የተጎዳውና ወደፊትም የሚጎዳው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው።

የውጭ ምንዛሬ ቀውስ አለ ምን ማለት ነው? ይህ ቀውስ የሚፈጠረው በሚከተሉት ሁኔታዎች ነው።
ሃብት ያላቸው ገንዘባቸውን ስላሸሹ (Capital Flight in the form of illicit outflow)፤ ብድር እየጨመረ ስለሄድና እዳው መከፈል ስላለበት፤ ከውጭ የሚሸመተው እየጨመረ፤ ለአገርና ለውጭ ገበያ የሚቀርበው ሳይጨምር ወይም እየቀነሰ ወይም የሚላከው እቃ የሚያስገኘው የውጭ ምንዛሬ ተሰርቆ እንዲሸሽ ስለተደረገ፤ ኢንቬስተሮች በአገሪቱ አመራር እምነት ስለሌላቸው ፈሰሳቸውን ለመቀነስ ስለተገደዱ፤ የብር የውጭ ምንዛሬ የመግዛት አቅሙ እየመነመነ ስለሄደ።

እነዚህ ግዙፍ ችግሮች ካሉ ምን አሉታዊ ሁኔታ ሊከሰት ይችላል፤ እንዴትስ ይፈታል?
ችግሩ በአጭር ጊዜ ሊፈታ አይችልም። አስር ዓመት ሊወስድ ይችላል። አቋራጭ መንገድ የለም (There is no quick fix). ከዚህ በፊት በሜክሲኮና በሌሎች የላቲን አሜሪካ አገሮች በ1994 እንደሆነው፤ ኢትዮጵያ እዳዋን ለመክፈል ካልቻለች ዲፎልት (እዳዋን የማትከፍል) ሆነች ማለት ነው። እዳዋን ካልከፈልች ወደፊት አበዳሪ አይኖርም። ኢንቬስትመንት ይቀንሳል። ኢትዮጵያ ያሏት አማራጮች አንድ፤ እዳን በሌላ እዳ መክፈል፤ ሁለት፤ አትራፊ የሆኑ የመንግሥት ኩባንያዎችን ሽጦ መክፈል፤ ሶስት፤ እዳዋ ይቅርታ እንዲደረግላት መደራደር ይገኙበታል።

ከባድ አማራጮች ናቸው። ኢትዮጵያ አሁን የምታስተናግደው አማራጭ ሁለተኛውን ነው። ይህ አማራጭ አወንታዊና አሉታዊ ገጽታዎች አሉት። የመንግሥት የሆኑትን በከፊል ወይም በሙሉ የግል የማድረጉ አማራጭ አወንታዊ ገጽታ በአጭሩ፤

  1. የግሉ ክፍል ውጤታማ፤ የትርፍ መሰረትና ተወዳዳሪ ስለሚሆን፤ የስራ እድል ስለሚፈጥር፤ የምርት ኃይሉን ለማጠናከር፤
  2. ተጨማሪ ካፒታል ስለሚገኝ፤ ይኼ ካፒታል ለኢንቬስትመንት ይውላል ተብሎ ስለሚታሰብ፤
  3. እዳን ለመክፈል የሚያስችል የውጭ ምንዛሬ ስለሚገኝና ሁኔታውን ለመቅረፍ አመቻች ስለሚሆን፤
  4. የግል ማድረጉ ቅልጥፍና ስለሚኖረው አገሪቱ ተወዳዳሪ የሆነ ኢኮኖሚ እንድትመሰርትና ወደ ውጭ ሊላክ የሚያስችል የኢንዱስትሪ መሰረት ለመጣል አመቻች ሁኔታ ለመፍጠር፤
  5. የግል ክፍሉ ጥናትና ምርምር፤ አዲስ የፈጠራ ዘዴዎች፤ ሳይንስና ቴክኖሎጅ ለመጠቀም ስለሚያስችለው፤
  6. ሕዝቡ በሽርክና የኢኮኖሚው እድገት ተሳታፊ እንዲሆን አመች ሁኔታን ስለሚፈጠር፤
  7. በመንግሥት በኩል የሚተዳደሩት ኩባንያዎች የአመራርና የሰራተኛ ጥራት ጉድለት ስላላቸው ይኼን ክፍተት ስለሚያሻሺል፤
  8. ለመንግሥት ካዝና ተጨማሪ የአጭር ጊዜ ገቢ ስለሚያስገኝ፤
  9. ሌብነትን፤ ጉቦን፤ ሙስናን፤ ከአገር የሚሸሸውን ግዙፍ ካፒታል ለመቀነስ ስለሚያስችል እና፤
  10. ኢኮኖሚውን ሊበራላይዝ (የገበያ ኢኰኖሚ) ለማድረግ እድል ስለሚሰጥና የምእራብ አገሮችን እምነት ስለሚሸምት። ይኼን ልቀበልና፤ አትራፊ የሆኑትን ድርጅቶች መሸጡ ለምን ተፈለገ፤ ማንን ለመጥቀም? የሚለውን ልገምግም።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የተለየ ትኩረት ስለሚያስፈልገው፤ ባለቤትነቱ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆኖ እንዲቆይ አሳስባለሁ። ምክንያቶቸ የሚከተሉት ናቸው።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ (ኢትዮጵያዊ/Ethiopian) መለያ፤ ዝናና ታዋቂነት ያለው የአገር ጥሪትና ቅርስ ነው፤
የድርጅቱ ዋና ስራ አስኪሃጅ እንዳለው፤ ይህ ጥሪት በግል ሲዋቀር አብረው የሚዋቀሩት የአየር ማደሻና ማሰልጠኛ ተቋሞች፤ የተያያዙ የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎችና ማምረቻዎች፤ በቶጎ አስኪ በተባለ አየር መንገድ በሽርክነት የተገኘው 40 በመቶ ድርሻ፤ በማላዊ አየር መንገድ የተያዘው 40 በመቶ ድርሻ፤ በዛምብያ አየር መንገድ የተያዘው 49 በመቶ ድርሻ፤ በቻዲያንና በጊኒያን የተያዘው ያልታወቀ

ድርሻ እና በፍጥነት እያደገ በሄደው በሞዛምቢክ የተቋቋመ አየር መንገድ ኢትዮጵያዊ በ 99 በመቶ ተመን ድርሻ የያዘው ሁሉ እንዲወቃቀርና ባለቤትነቱ እንዲሸጋሸግ የሚያስገድድ ሁኔታ ይፈጠራል።
እነዚህ ሁሉ ስኬታማ የሆኑት ኢትዮጵያዊ ዝነኛ ታሪክ ስላለው፤ አገልግሎቱ በዓለም የታወቀ ስለሆነ ነው።

ይህን የኢትዮጵያ መለያ በከፊል ሆነ ሌላ ለአጭር ጊዜ የውጭ ምንዛሬ ቀውስ ማስተካከያ ለማድረግ በሚል ፈሊጥ፤ ባለቤትነቱን ማዛባት አደገኛ ከመሆን አልፎ የአገሪቱን ጉረሮ እንደ ማነቅ ነው።
አትራፊ የሆነን ድርጅት መሸጥ የማህበረሰባዊና ብሄራዊ ፋይዳ የለውም።

ኢትዮጵያዊ በ2016/2017 $2.7 ቢሊየን ጠቅላላ ገቢና $232 ሚሊየን ንጥር ትርፍ ለአገሪቱ አስገብቷል። ይህ ከሩብ ቢሊየን ዶላር ገቢ ፍይዳ አለው። ድርጅቱ ተጠናክሮ፤ ራሱን ከሌቦች አጽድቶ እንዲቀጥል መደረግ አለበት።
በዚህ መስፈርት ብቻ ስገመግመው ድርጅቱ በኢትዮጵያ ሕዝብ ባለቤትነት ይቆይ የሚለው አቋም ያሸንፋል።

ከዚህ በፊት፤ ዓለም ባንክና አይኤምኤፍ ግፊት አድርገው ጠ/ሚንስትር መለስ “ሰራተኞቹን ማን ደሞዝ ይከፍላቸዋል፤ ለአገር የሚገባውን ገቢ ማን ያሟላዋል፤ ገንዘቡ ከየት ይመጣል” ብሎ ያስጠነቀቀውን ማስታወስ ይጠቅማል። በኔ ጥናትና ምክር፤ ይህን ድርጅት በከፊል ሆነ በሙሉ የግል ማደረግ ከማንም ፓርቲና መሪ በላይ ነው። ውሳኔው የኢትዮጵያ ሕዝብ እንጅ የኢህአዴግ ሊሆን አይችልም። ይህ ፓርቲ እስካሁን ያባከነው ሃብት ይበቃል!!!

ለማጠቃለል፤ አንድን ስኬታማ ድርጅት እንደ ገና ማዋቀር፤ ባለቤትነቱን ማዘዋወር ቀላል ነው፤ መተካት ግን አስቸጋሪ ነው። የመንግሥት የሆኑትን በከፊል ወይም በሙሉ የግል የማድረጉ አማራጭ አሉታዊ ገጽታ በአጭሩ፤ ስለ አየር መንገዱ ያቀረብኩት እንዳለ ሆኖ፤
  1. ማንኛውም አገር ትርፍ የሚያስገኝ፤ ለብዙ ዜጎች የስራ እድል የሚሰጥ፤ የውጭ ምንዛሬና የአገር ውስጥ ገቢ የሚሰጥ የመንግሥት (የሕዝብ) ድርጂትን በከፊልም ሆነ በሙሉ ለግል ክፍሉ አይሸጥም። መሸጡ የአጭር ጊዜ ጥቅም ሊኖረው ቢችልም፤ የረዢም ጊዜ ጉዳቱ ካጭር ጊዜ ጥቅሙ ያመዝናል።
  2. የኢትዮጵያ መንግሥት እንደ ኢትዮጵያ አየር መንገድ ስትራተጂክ (መተኪያ የሌላቸው) አትራፊ ኩባንያዎችን መንከባከብ እንጅ በከፊል ሆነ በሙሉ ወደ ግል ይዞታ ማስተላለፍ አይገባውም፤ ይህ ፖሊሲ አደገኛ ነው።
  3. አትራፊ የሆነ የመንግሥት (የሕዝብ) ኩባንያ የግል ሲሆን ተጠቃሚው ሕዝቡ የሚሆንበት ሁኔታ አልተፈጠረም። ሽርክና ይኖራል የሚለው የተሳሳተ ጽንሰ ሃሳብ አለ። አየር መንገዱን ሆነ ሌሎችን አትራፊ ኩባንያዎች የሚገዛቸው የገንዘብ አቅም ያለው ነው። ገንዘብ ያለው የአገር ውስጥ ኢንቬስተር በሌብነት፤ በሙስና፤ በውጭ ምንዛሪ ማሸሽ የሚጠረጠር ከሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ አሁንም የበላይነቱን የሚይዘው ይኼው ቡድን ወይም መደብ ይሆናል።
  4. የግል ክፍሉ የበላዩን ወይም ከፊሉን ድርሻ በሚይዝበት ጊዜ ትኩረቱ ከትርፍ ላይ ስለሚሆን፤ ሰራተኞችን የመቀነስና የማባረር መብት አለው። እነዚህን ሰራተኞች ማን ይቀጥራቸዋል፤ መንግሥት?
  5. ጥናቶችና ምርምሮች የሚያሳዩት የመንግሥት የነበሩ ድርጅቶች ወደ ግል ሲዘዋወሩ ለህብረተሰቡ የሚሰጡት አገልግሎት ይቀንሳል ወይም ሊያጠፋ ይችላል። ለምሳሌ፤ ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው ግለሰቦች የውሃ፤ የቴሌፎን፤ የመብራት አገልግሎት በዝቅተኛ ዋጋ ያገኙ ከነበረ ወይም ወደፊት እንዲያገኙ ከተፈለገ ድርጅቶች የግል ሲሆኑ የመግዛት አቅማቸው ዝቅ ሊል ይችላል። ሁኔታውን የሚያባብሰው ወድድር ስለሌለ ነው። ይህ ችግር የሚፈታው ቅድመ ሁኔታዎች፤ ሕጉና መምሪያው መሠረት ሲይዝና ብሄራዊ ተቋማት ሲመሰረቱ ነው።
  6. የግል ክፍሉ ግልጽነት፤ የማወራረድ ልምድ፤ ሃላፊነት፤ የማህበረሰባዊ አገልግሎት ባህል ሲያሳይ፤ የገበያ ውድድር ሲመሰርት፤ ዲሞክራሳዊ የሆነ ውድድር (Stock Market) ሲኖርና፤ ተጠቃሚው ኅብት ያለው ብቻ ሳይሆን ትንሽ ካፒታል ያለው ጫማ ጠራጊ ሆነ ሱቅ በደረቴ ያለው የሚሳተፍበት አመች ሁኔታ ሲመቻች ነው። ይህን ለማድረግ፤ ለማመቻቸት የሚችለው አካል የፌደራሉ መንግሥት ነው። ይህ ስራ ገና አልተሰራም፤ ከተሰራ ድብቅ ነው። ግልጽነት ይኑር።
  7. እርግጥ ነው፤ በግል ድርጅቶች ዓለም ስንፍና አይኖርም ይባላል፤ በአብዛኛው ትክክል ነው። በመንግሥት የተያዙም ድርጅቶች ሰራተኞች ለአገርና ለሕዝብ ስለሚሰሩ ጠንካራና ታታሪ የማይሆኑበት ምክንያት የለም፤ ለምሳሌ፤ አየር መንገድ፤ መብራት ኅይል፤ መምህራን። ለአገርና ለሕዝብ የሚሰጥ አገልግሎት ዋጋና ክብር ሊሰጠው ይገባል (የጃፓን ሞዴል) ። የመንግሥት የሆኑ ድርጅቶች፤ ለሕዝብ ቅልጥፍናና ጥራት ያለው አገልግሎት የመስጠት ግዴታቸው ከፍ እንዲል ማድረግ ያስፈልጋል። መንግሥት በኢኮኖሚው፤ በተለይ፤ በመሰረተ ልማትና በማህበረሰባዊ አገልግሎት ከፍተኛ ሚና አለው። ስኳር ለማምረት ግን ሚናው አይደለም። ለሌብነት ግን አመች ሁኔታ ፈጥሯል። ጠ/ሚንስትር ዶር አብይ ትኩረት ሊሰጧባቸው ከሚገባቸው ጉዳዮች መካከል በጣም ኋላ ቀር የሆነውን የሰው ኃይል አቅም መገንባት ነው (Managerial, professional and technical capacity building). ይህ ትኩረት ወሳኝ ነው።
  8. መንግሥት ለህይዎት አስፈላጊ ለሆኑ፤ መብራት፤ ውሃ፤ ኤሌክትሪክ አገልሎቶች የዋጋ ክትትልና ቁጥጥር ግዴታ አለበት።
  9. ህወሓት መራሹ ፓርቲ፤ በተለይ ህወሓትና ሲቆጣጠረው የቆየው መንግሥት በኢኮኖሚው ላይ ያላቸው ሚና የተዛባና የግሉን ክፍል ያደከመ፤ ለሕዝብ አገልግሎች ደንታ ቢስ የሆነ፤ ለሌብነት፤ ለጉቦ፤ ለሙስናና ከአገር ለሚሸሽ ገንዘብ ዋናውን ሚና በመጫዎት፤ መዋቅራዊ ተግዳሮት የፈጠረ ነው። የእድገት ምሰሶዎችን በበላይነት ይዞ ለሃያ ስምንት ዓመታት ቀውሶችን ፈጥሯል። ይህን ለመፍታት ጥራት ያለው አመራር ያስፈልጋል።
  10. እድገቱ መሰረታዊና መዋቅራዊ ለውጦችን ለማምጣት አልቻለም። የሕዝቡ ፍላጎት በአገር ተከል የምርት ውጤቶች ሊደገፍ አልቻለም። በ2017 አገሪቱ ከውጭ የሸመተችው የውጭ ምንዛሬ መጠን $19 ቢሊየን ነው፤ እዳው $25 ቢሊየን ደርሷል። ወደ ውጭ የላክችው መጠን $1.7 ቢሊየን ሲሆን የምትሸምተው ከምትልከው አስራ ስምንት እጅ ይበልጣል። የምትሸምታቸው እቃዎች መሳሪያዎች፤ መኪናዎች፤ አውሮፕላኖች፤ መድሃኒቶች፤ ነዳጅ፤ ምግብና የምግብ ዘይቶች፤ ብዙ የቅንጦት እቃዎች ይገኙበታል። ሰሊጥ፤ ኑግና ሊሎች የምግብ ዘይቶች ለማምረት እድል ያላት አገር ራሷን አለመቻሏ የእድገቱ ትኩረት የተዛባ መሆኑን ያሳያል። የኢኮኖሚው መዋቅር ገና አልተለወጠም፤ ይህም ለውጭ ምንዛሬው ቀውስ ግብዓት አለው። አገሪቱ ለውጭ ገበያ የምታቀርበው ቡና፤ ቅጠላ ቅጠል፤ ስጋ፤ ቆዳና ከቆዳ የተሰራ፤ ጨርቃ ጨርቅ፤ ወርቅና ሌሎች የመአድን ውጤቶችን ነው። የንግዱ ሚዛን ሁሌም የተዛባ የሚሆነው ክፍተት ስላለ ነው። በዚህ መስፈርት፤ አገራችን ከ145 አገሮች መካከል 133ኛ ናት። ይህ የተዛባ የንግድ ሁኔታ የፖሊሲና የመዋቅር ማስተካከል መፍትሄ ካላገኝ የሕዝብ የሆኑትን ድርጅቶች መሸጥ ችግሩን አይፈታውም።
  11. መደጋገም አይሁን እንጅ ፓርቲዎች ከኢኮኖሚው ስራ ሙሉ በሙሉ መውጣት አለባቸው። በቀጥታም ሆነ በጀርባ የመሰረቷቸው፤ እንደ ኤፈርትና ሜቴክ ያሉ ኩባንያዎች በሙሉ የፋይናንስ ሁኔታዎችን ፈሰስና ግልጽ ማድረግ አለባቸው (Full Disclosure and Transparency) ፤ የተበደሩትን የባንክ ብድርና የውጭ ምንዛሬ እንዲከፍሉ፤ ካልከፈሉ ቢያንስ የሕዝብ ኃብት ማባከናቸውን እንዲቀበሉ ማድረግ ችግሩ ወደፊት እንዳይደገም ትምህርት ይጠቅማል።
  12. ማንኛውም ማወቃቀር የኢትዮጵያንና የሕዝቡን ዘላቂ ጥቅም ማስከበር ይኖርበታል (The Public Interest Must be the Overarching Guide in privatization).
  13. በከፊል ሆነ በሙሉ የግል ይሁን ሲባል ያለ አግባብ ኅብታም የሆኑትን ተጨማሪ ሃብት ለመለገስ መሆን የለበትም። ይህ ከሆነ የዱሮው ሶቪየት ህብረት ፈርሶ ጥቂት ሌቦች (Oligarchs) የበላይነቱን እንደያዙት ይሆናል። ያለው ቀውስ ይባባሳል። ሕዝብ እንደ ገና ይንሳል። እርጋታና ሰላም አይኖርም። 
ችግሮቹን ለመፍታት ምን አማራጮች አሉ? ከአገር በገፍ ተሰርቆ የሸሸው $30 ቢሊየን እንዲመለስ ከፍተኛ ጥረት ይደረግ፤ አምሳ በመቶው ቢመለስ $15 ቢሊየን ቀላል አይደለም። የውጭ ምንዛሬ ሰርቀው ያሸሹ በፈቃዳቸው ገንዘቡን ወደ አገር ለመመለስ ፍላጎት ካላቸው ባለቤትነታችው ቢከበርና የውጭ ምንዛሬውን ተጠቅመው ከፍተኛ ዋጋና ጥቅም ያላቸውን፤ የሕዝቡን የፍጆት ፍላጎት የሚያሟሉ (የምግብ ዘይት፤ ሳሙና፤ የቤት እቃዎች፤

ጨርቃ ጨርቅና የመሳሰሉ (Deliberate Import Substitution) እና፤ የአገሪቱን የውጭ ገበያ ተውዳዳሪነት ለማጠናከር (Export Promotion) እና የስራ እድል ለመፍጠር ፋብሪካዎችን/ኢንዱስትሪዎችን እንዲያቋቁሙ ጥሪ ቢደረግላቸውና ምንም አይነት ቅጣት እንደማይደስባቸው ዋስትና ቢሰጣቸው መልካም ነው። እነሱ ተከብረው አገራቸውን ያስከብራሉ።
መንግሥት ከአበዳሪዎች ጋር በመደራደር የሚክፈለውን እዳ እንደገና እንዲዋቀርና ለአገሪቱ በሚጠቅም ሁኔታ የክፍያው ወለድና መጠን እንዲቀንስ፤ እዳው በረዢም ጊዜ እንዲከፈል ማድረግ ይኖርበታል። በገዢው ፓርቲ፤ በተለይ በህወሓት የተመሰረቱት እንደ ኤፈርት ያሉ ሞኖፖሊዎች ከባንኮች የተበደሩትን ብድርና ከውጭ በልዩ ልዩ ዘዴዎች በልማት ስም ያገኙትን የውጭ ምንዛሬ እንዲከፍሉ ማስገደድ። አስፈላጊ ከሆነ ያላቸውን ሃብት (Assets) እንዲሸጡና እዳቸውን እንዲያወራርዱ ማስገደድ። ሌሎች ተመሳሳይ ድርጅቶችም ተመጣጣኝ ግዴታ እንዲኖራቸው ማድረግ። ማንም ድርጂት ወይም ግለሰብ ከሕግ በላይ እንዳልሆነ ማሳየት።

5. ከአሁን ጀምሮ ማንኛውም የመንግሥት ባለሥልጣን የውጭ ምንዛሬ እንዳያባክን ቃል ኪዳን ማስገባት፤ የሚያባክነውን ከስራው ማስወጣት።
6. የአገር ውስጥ እንቬስተሮች ነጻ ሆነው፤ ከፍተኛ ድጋፍ ተሰጥቷቸው በቴሌፎን፤ በመብራትና ሌሎች ክፍሎች አገልግሎት እንዲስጡ ኢኮኖሚውንና ገበያውን ክፍት ማድረግ።
7. የአገር ውስጥ ኢንቬስተሮች፤ ዲያስፖራውን ጨምሮ፤ የግል የአየር መንገድ አገልግሎት እንዲያቋቁሙ ማበረታት::
8. መንግሥት ለወጣቱ ትውልድ ልዩ ትኩርትና ድጋፍ ሰጥቶ የዘመናዊ እርሻ እንዲመሰርት ማድረግ፤ ግብአት እንዲሆን ከዓለም ባንክ ያለ ምንም ወለድ፤ በሃያ አምስት ዓመት የሚከፈል $300 ሚሊየን መበደር፤ ለወጣቱ ተጠቃሚ የአቅም ግንባታ ማድረግ፤ ልዩ ትኩረት የሚሰጣቸውን ወደ ውጭ የሚላኩና የውጭ ምንዛሬ የሚያስገኙ የምርት ውጤቶች በባልሞያዎች አስጠንቶ ማቅረብ::
9. የኢትዮጵያ የወደፊት እድል የሚወሰነው በሕዝቧ፤ በተለይ በወጣቱ ትውልድ ተሳትፎ፤ ጥራት፤ ብቃትና ባለቤትነት ነው። ይህ ሕዝብ ለአገሩ ተቆርቋሪ፤ ታታሪ፤ ፈጣሪ፤ ብቃት፤ ጥራት፤ አምራችና አገልጋይ የመሆን ችሎታ እንዳለው አስመስክሯል። ይህን ኃይል በስብሰባ፤ በግምገማ፤ በፓርቲ ታማኝነት ያመከነው ህወሓት መራሹ ስርዓት ነው። ስንት ቢሊየን ሰዓቶች፤ ስንት መቶዎች ሚሊየን ብር በየዓመቱ ለስብሰባና ለግምገማ እንደባከነ ለመተመን አያዳግትም።
10. የአሁኑ ለውጥ መሰረታዊ ይዘቶች ስላሉት፤ ዲያስፖራው ማንኛውንም የውጭ ምንዛሬ እቀባ እንዲያነሳና ከመቸውም በበለጠ ደረጃ የውጭ ምንዛሬ በብሄራዊ ባንክ አማካይነት እንዲገባ ያልተቆጠበ ጥረት ማድረግ፤
11. መንግሥት የተፈጠረውን ሰው ሰራሽ የውጭ ምንዛሬ እጥረት ለመወጣት ወዳጅ መንግሥታት የውጭ ምንዛሬ ድጋፍ እንዲሰጡ ማበረታት፤ ከውጭ በገፍ የሚሸመተውን የቅንጦት እቃ ማቆምና ወደ ውጭ የሚላከውን እቃ ብዛትና ጥራት መጨመርና፤
ዓለም ባንክ፤ አይ ኤም ኤፍ፤ የምእራብ አገሮች፤ በተለይ አሜሪካ የተዘረፈውን ግዙፍ ሃብት ለመከታተልና እንዲመለስ እውቀቱና አቅሙ ስላላቸው፤ ክትትል እንዲያደርጉና ገንዘቡ እንዲመለስ ከአሁን ውይይትና ስምምነት ማድረግ።
13. ዲያስፖራው በያለበት የሌቦችን ስምና የውጭ ምንዛሬና ሌላ አግባብ የሌለው ኃብት በየአገሩ ያስቀመጡትን በማስረጃ ተደግፈው ለጠ/ሚንስትሩ ቢሮ ብቻ እንዲልኩ ማበረታታት።

እነዚህን አማራጮች ለማቅረብ የተገደድኩበት ምክንያት ህወሓቶችና አጋሮቻቸው ለውጭ ምንዛሬው ብክነትና ቀውስ ተጠያቂ መሆናቸውን በመረጃ ለማሳየት ነው። አትራፊ የሆኑትን የመንግሥት ድርጅቶች በከፊልም ሆነ በሙሉ የግል ከማድረግ ይልቅ እንደ ኤፎርትና ሌሎች ከሕዝብ በተነጠቀ ካፒታል የተቋቋሙ ኩባንያዎችን የግል እንዲሆኑ ጫና ማድረግ ይመረጣል።

ይህን ስል፤ አንዳንድ የመንግሥት የሆኑ ኩባንያዎች ጥናትና ምርምር ተደርጎባቸው በከፊልም ሆነ በሙሉ የግል እንዲሆኑ ማድረጉ አማራጭ መሆኑን እቀበላለሁ። ሆኖም፤ ቅድመ ሁኔታዎች መመሰረትና ግልጽ መሆን አለባቸው።

ለማጠቃለል ህወሓት መራሹ ቡድንና ተባባሪዎች የዘረፉትን የውጭ ምንዛሬ መመለስ አለባቸው።

No comments