Latest

የሕዝብና የመንግሥት ሀብት በመመዝበር በሚጠረጠሩ ላይ ምርመራ መጠናቀቁ ተጠቆመ - ዮሐንስ አንበርብር

የመንግሥት

በተደራጀና በቅንጅት የሕዝብና የመንግሥት ሀብት መዝብረዋል ተብለው በተጠረጠሩ ላይ፣ ሕጋዊ ዕርምጃ ለመውሰድ ምርመራ መጠናቀቁን የሪፖርተር ምንጮች ገለጹ፡፡

የፌዴራል ፖሊስና የምርመራ ቢሮና የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽሕፈት ቤት በተለዩ ዘርፎች ላይ ሰፊ ምርመራ ሲያካሄዱ እንደነበር፣ ምርመራውም በአሁኑ ወቅት በመገባደድ ላይ መሆኑን ለጉዳዩ ቅርብ የሆኑት ምንጮች ገልጸዋል፡፡

ሲካሄድ የቆየው የወንጀል ምርመራ በዋናኛነት ትኩረት ያደረገው ‹‹የተደራጀ ሌብነት››፣ ወይም በተለያዩ አካላት በቅንጅት የሕዝብና የመንግሥት ሀብት ላይ ምዝበራ አካሂደዋል ተብለው በቅድሚያ በተለዩ ዘርፎች ላይ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በጥቂት ሳምንታት ውስጥም ተጠርጣሪዎችን ይዞ ለሕግ የማቅረብ ተግባር እንደሚከናወን ምንጮች አስረድተዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ከሁለት ሳምንታት በፊት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተገኝተው በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ በሰጡት ማብራርያ፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ‹‹የኢኮኖሚ ሻጥር›› በተደራጀ መንገድ እየተፈጸመ እንደሆነና ‹‹የተደራጀ ሌብነት›› በአገሪቱ ውስጥ የአምስተኛ መንግሥት ባህሪ ይዞ ስለመከሰቱ መናገራቸው ይታወሳል፡፡

‹‹እነዚህ አፀያፊ ተግባሮች እንዲታረሙ ለማድረግ መንግሥት አስፈላጊ ዕርምጃ ይወስዳል፤›› ሲሉ በወቅቱ የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ መሠረታዊ ችግር ታይቶባቸዋል ያሏቸውን አካባቢዎች ዘርዝረው ነበር፡፡

በውኃ፣ የኤሌክትሪክ፣ የቴሌኮምና የመንገድ የመሳሰሉት መሠረታዊ ልማቶች ላይ የሚታየው የጥራት ችግር አንዱ ቁልፍ ምክንያት፣ ጥራታቸው በወረደ ጥሬ ዕቃዎች መገንባታቸው እንዲሁም በአገልግሎቱ አቅራቢዎች ውስጥ ሙሰኝነት፣ አድልኦና የግል ጥቅምን ማስቀደምና የአሻጥር ድርጊቶች መሆናቸውን ተናግረው ነበር፡፡

በተጨማሪም በፍትሕ አስከባሪ አካላት አማካይነት ግለሰቦችንና ድርጅቶችን ለመጥቀም ሲባል ሕገወጥ እንቅስቃሴ እንደሚደረግ መናገራቸው ይታወሳል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይኼንን ቢሉም በመገባደድ ላይ ያለው ምርመራ ያተኮረባቸውን ዘርፎች ምርመራው ተጠናቆ ይፋ እስኪሆን ድረስ ምንጮች ይፋ ከማድረግ ተቆጥበዋል፡፡

No comments